You are here: HomeSocial Issues የወንዶች እና የሴቶች ሙግት፡   ቀጥሮኝ በሰዓቱ የሚገኝ ሰው አማረኝ?

የወንዶች እና የሴቶች ሙግት፡   ቀጥሮኝ በሰዓቱ የሚገኝ ሰው አማረኝ?

Written by  Tuesday, 06 May 2014 00:00

እናንተዬ ሰሞኑን ደግሞ እንዲሁ ከመሬት ተነስቼ ሆድ ይብሰኛል። “ያለተመረመረ ህይወት ሊኖር አይገባውም” ፤ “ሰው በልቡ እንደሚያስበው እንዲያው ነው” የሚሉትን የጥበብ ቃላት አስብና በሬን ዘግቼ፤ ብዕሬን አሹዬ ልሙጥ ወረቀት ከፊቴ ከምሬ፤ የአዕምሮዬን ጓዳ እበረብራለሁ። አንዳንድ ጊዜ  በዕፍረት የሚያሸማቅቅ፤ አንዳንዴ ደግሞ በትዕቢት ልብን የሚያሳብጥ ነገር ይገጥመኛል። በተለይ ለጊዜ ካለኝ ስስት የመነጨ ነው መሰለኝ “የቀጠሮ ጉዳይ” ያሳስበኛል። የእኔን ለሌላ ጊዜ እናቆየውና ፤ለዛሬ ግን የሴት እና ወንድ ወዳጆቼን ሙግት ከገሚሱ ጋር በአካል ከሌሎቹ ጋር በምናብ ላሳያችሁ ነው።እንዲያው በተለየ ከተቃራኒ ፆታ (ከፍቅር ጓደኛቸው) ጋር ላላቸው ቀጠሮ የሚሰጡት ትኩረት ምን ይመስላል?  ወንድ ወዳጆቼ ሆኑ እንስት ወዳጆቼ ቀጠሮ ላይ እንዴት ናቸው? በጥቅሉ እኔ እና ወዳጆቼ የምንማከረው፡-  ቀጥሮኝ በቃሉ የሚገኝ ሰው አማረኝ እየተባባልን ነው? (እናንተስ አላማራችሁም ?)

 

ከጓደኞቼ ልጀምር! አንዱ ወዳጄ ድንገት ፊቴ  ድቅን አለብኝ ። ይሄ ወዳጄ ‘ነገ ከቀኑ ሰባት ሰዓት ላይ እንገናኝ’ ካለ እንዳማይመጣ ፍንጭ መስጠቱ፣ ‘ዕደውላለሁ’ ካለ እንደማይደውል ለማወቅ ምንም ጥረት አያሰፈልጋችሁም። ይሄ ወዳጄ ፍልቅልቅ እና ተጫዋች በመሆኑ ብንወደውም በ“ቀጠሮ ጉዳይ” ግን ሁሌ የትችታችን ማዕከል ነው። ታዲያ “ለምን ቀረህ?” ብላችሁ ደፈር ብላችሁ ብትጠይቁት “እቤቴ ቁጭ ብዬ!” ብሎ እውነቱን ፍርጥ አድርጎ ያስደነግጣችል። ቀጠሮ በሌላችሁ ቀን ግን ይሄ ወዳጄ ያለችሁበትን ፈልጎ ድንገት ፊታችሁ  ድቅን ብሎ ሊያስደነግጣችሁ ይችላል። አሁንም ቢሆን እሱም መቅጠሩን፣ እኛም መጠበቃችንን አልተውንም አንድ ቀን ቢሳካለት እና በቃሉ ቢገኝ ብለን።  እሱን ሳገኘው “ቀጥሮኝ በሰዓቱ የሚገኝ ሰው አማረኝ?” እላለሁ ለራሴ። 

 

ሌላ ዕንስት ወዳጄ ደግሞ ፊቷን ኮስተር አድርጋ አይን አይን እያየችኝ “ወንድ ልጅማ መጠበቅ አለበት። ምክንያቱም ወንድ ልጅ እኮ ፊቱን ታጠብ ብሎ መውጣት ይችላል፤ ሴት ልጅ ግን እንደዛ ማድረግ አትችልም። አለ አይደል መቆነጃጀት አለባት ። ቢያንስ በትንሹ 30 ደቂቃ መታገስ አለበት!” ባይ ነች። ሌላው ወዳጄ ግን በንዴት እየተንቦገቦገ “ወንድ ልጅ ‘መቆነጃጀት’ አይወድለትም ያለሽ ማን ነው? ስንፍናችሁን ከቀጠሮ ጋር አታያይዙት!” ይላታል። ይሄ ወዳጄ ቀጠሮን በተመለከተ 5/15 የሚባል ህግ አለው። ይህንንም ሲያብራራ “የትኛውንም ቀጠሮ  ስፍራ ላይ  አስፈላጊውን መስወዕት ከፍዬ 5 ደቂቃ ቀድሜ እገኛለሁ። 15 ደቂቃ እጠብቃለሁ ከዛ ወደ ጉዳዬ ነው የምሄደው!” ይላል።  ከላይ የጠቀስኳት ወዳጄ ግን በዚህ አትስማማም “ዕስቲ ሌላውን ተወው እንዲያው ምን ችግር አጋጥሟት ነው እንኳን አይባልም?” ብላ ትሞግተዋለች።  ይሄ የሚቀርባቸው ዕንስቶች በቀጠሮ ላይ ያላቸው ለዘብተኝነት የማይጥመው ወዳጄ “እኔ በጦር አላሰፈራራት የሚፈጅበትን ጊዜ አስልታ አትቀጥረኝም እንዴ? ቀጥሮኝ በቃሉ የሚገኝ ሰው እኮ ነው ያማረኝ?” ይላል።

 

አንድ ግን በቅፅል ስሙ “ትዕግስቱ” የምንለው ወዳጃችን ደግሞ አለ ፡፡ ይሄ ወዳጄ ፍቅር ቢጤ ይዞት ነው መሰለኝ አንድ “ከማትመስለው” ሴት ጋር ይወዳጃል። ይህች ልጅ  ከእሱ አስበልጣ ‘ፌስቡክን’ የምትወድ  መሆኗን ከጓደኞቹ ቢሰማም፤ እሷ ግን ሁል ጊዜ የምትነገርው እንደማይመቻት እና ‘ቢዚ’ እንደሆነች ነው። “አንዳንድ ጊዜ” ይላል ይሄ ወዳጄ በንዴት እየተብከነከነ “በስንት ደጅ ጥናት እንቀጣጠር እና ከተገናኝን በላ ‘ስራ አለኝ ከ15 ደቂቃ በላ እሄዳለሁ’ ትለኛለች፡፡ የመጣችው ዕኮ አንድ ሰዓት አሳልፋ ነው።” ይላል። አንድ ጊዜ የተከሰተውን ሲናገር ግን ይዘገንናል “ከተቀጣጠርንበት ሰዓት በላ ለሁለት ሰዓት ያህል መስሪያ ቤታቸው በር ላይ ልክ እንደ ኢያሪኮ ግንብ ሳፈጥ አምሽቼ፤ ቢቸግረኝ ደውልኩ ቆይ ‘ትንሽ ጠብቀኝ’ ብላኝ ከሰላሳ ደቂቃ በላ መጣች። የረባ ይቅርታ እንኳን ሳትጠይቀኝ  ወደ ቤት ሸኘኝ አለችኝ?” ይላል የአግራሞት ሳቅ እየሳቀ። እኛም ታዲያ ከዚች ልጅ ጋር እሰከ አሁን በመቆየቱ ነው “ትዕግስቱ” ያልነው።  ታዲያ ይሄ ወዳጄ “ቀጥራኝ የምትገኝ ሴት ናፈቀኝችኝ?” ቢል ይፈረድበታል!

 

ሕሊና በአንድ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት ውስጥ ነው የምትሰራው ቀጠሮን በተመለከተ  ከላይ የጠቀስኳቸው ዕንስቶችም ሆነ ወንዶች በሚያደርጉትም በሚሉትም አትስማም። “ ወንዶችን መጠበቅ አለባቸው የሚለውን አሳምሽን [ቅድመ ዕሳቤ] ሆነ ተቃራኒውን አልስማማበትም። ሁላችንም[ወንዶችም ሴቶችም] በቃላችን መገኘት አለብን። በተለይ ሴቶች ቀጠሮ ስንይዝ በደንብ ልናስብበት ይገባል። ማንም እንዲወደኝ ብዬ አልኖርም ! ቢወደኝ ጥሩ ባይወደኝ ምን ይደረጋል! ለዕሱ ብዬ የማምነበትን አልሻራርፍም!” ትላለች ፈርጠም ብላ፡፤

 

እናንተዬ ወንዶች ሴቶችን፤ ሴቶችም ወንዶችን ቀጠሮ ላይ ችግር አለባቸው ብለው ይወነጃጀላሉ። ይሟገታሉ። ወጣም ወረደም ግን እኔን የናፈቀኝ ሙግት ሳይሆን “ቀጥሮኝ በቃሉ የሚገኝ ወንድ ፤ ቀጥራኝ በሰዓቱ የምትገኝ ሴት” ማግኘት ነው። የዕናንተስ “የቀጠሮ ህይወት” እንዴት ይሆን ? እባካችሁ ፃፉልኝ እና በዚሁ መድረክ ላይ እንማከርበት!

 

ይርዳና! 

Read 9673 times Last modified on Tuesday, 06 May 2014 15:50
Abinet Ababu

I am Abinet Ababu a disciple, a husband and a father of two. A graduate of for Evangelical Theological college (ETC) in Bible Translation and Literacy. A student at at Africa Nazarene University (Nairobi, Kenya). A Bible school teacher, speaker and writer. An Interpreter by trade (to Amharic,English to Ormiffa -pending). 

Website: abinetababu.wordpress.com Email This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it.

Nahu's Corner

 

 

 

.

Right Now

We have 137 guests and no members online

About Us

Semayawi Thought is an online magazine published in Amharic and English, focused on contents to spiritual and personal growth.