You are here: HomeOpinionsዘንድሮ ነቢይ አለ? ነቢይ ማለት ምን ማለት ነው?

ዘንድሮ ነቢይ አለ? ነቢይ ማለት ምን ማለት ነው?

Written by  Tuesday, 19 July 2016 00:55

‹‹ነቢይ›› የሚለውን ቃል ፍቺና ተያያዥ ሀሳቦች ዴቪድ ፔትስ የተባሉ ጸሐፊ እንደሚከተለው ይገልጻሉ፡-

 

‹‹ነቢይ ማለት የወደፊቱን የሚናገር ወይም የሚያመለክት ማለት ነው፡፡ ፕሮፌቴስ የሚለው የግሪክ ቃል ከሁለት ጥምር ቃሎች የተገኘ ሲሆን እነዚህም ፕሮ (የወደፊት) እና ፌሚ (እናገራለሁ) የተባሉት ቃሎች ናቸው፡፡ ስለዚህ ነቢይ የሚለው ቃል ከመሆኑ አስቀድሞ ሊሆን ያለውን ነገር የሚያመለክት ማለት ነው፡፡

 

በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ግን ነቢይ የሚለው ቃል አጠቃቀም ከዚህ ትርጉም የሚያልፍ ነው፡፡ በብሉይም ሆነ በአዲስ ኪዳን ነቢይ እንደ ሰውየው ሆኖ ስለ ሌላ ሰው የሚናገር ወኪል (አፍ) ነው፡፡ የዚህ ጥሩ ምሳሌ በዘጸአት 7፡1 ላይ ይገኛል፡፡

 

‹‹እግዚአብሔርም ሙሴን አለው፦ እይ፥ እኔ ለፈርዖን አምላክ አድርጌሃለሁ ወንድምህም አሮን ነቢይ ይሆንልሃል።››

 

አሮን በሙሴ ስም ስለሚናገር የእሱ ነቢይ ተብሎ ተጠርቷል፡፡ በዚህ ትርጉም መሠረት ነቢያት ከእግዚአብሔር ሰምተው የሚቀበሉና ያንን የተቀበሉትን መልእክት ለሌሎች የሚያደርሱ ናቸው፡፡ በእግዚአብሔር ስም ይናገራሉ፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ነቢይ የሚለው ቃል ጥቅም ላይ የሚውለው በዚህ ትርጉም መሠረት ነው፡፡ እግዚአብሔር የወደፊቱንም ሁሉ አዋቂ ስለሆነ እርሱ በገለጠላቸው ጊዜና መጠን ነቢያት ስለ ወደፊቱ ሊናገሩ ይችላሉ፡፡ ይሁን እንጂ ነቢያት አብዛኛው መልእክታቸው በእግዚአብሔር ስም ለትውልዳቸው መናገር ነው፡፡ በመሆኑም ስለ ነቢያት አገልግሎት ብሉይንና አዲስ ኪዳንን ስንመረምር የቃሉን ሁለት ትርጉሞች ልብ እንበል፡-

 

  1. አብሣሪ፡- የእግዚአብሔርን እውነት የሚያውጅ
  2. አመልካች፡- ስለ ወደፊቱ የሚተነብይ››[1]

 

በዘመናት መካከል ሰዎችን ለራሱ የሚያስነሳው እግዚአብሔር ነው፡፡ በምድራችን ላይ ሰዎች አልተነሱም ወይ? ተነስተውም ነበር፤ እየተነሱም ነው፡፡ ብዙ ነቢያት መኖራቸውን ከሚያምኑት ወገን ነኝ፡፡ በዚህ ጽሑፍ የዘንድሮውን የነቢያት አብዮት አልተቃወመም ለመባል ሰፊ የአድናቆት ሽፋን አልሰጥም፡፡ ግን ነቢያት እንዳሉ አምናለሁ፡፡

 

የአዲስ ኪዳን መጽሐፍ ሲናገር እግዚአብሔር ለቤተ ክርስቲያን ከሰጣቸው ስጦታዎች መካከል የነቢያት አገልግሎት አንዱ ነው፡፡

   

‹‹እርሱም አንዳንዶቹ ሐዋርያት፥ ሌሎቹም ነቢያት፥ ሌሎቹም ወንጌልን ሰባኪዎች፥ ሌሎቹም እረኞችና አስተማሪዎች እንዲሆኑ ሰጠ፤›› ኤፌሶን 4፡11

 

በዘመናት መካከል የተነሱ ሰዎችን አካሄድ ማረም፣ መፈተን፣ በተገቢው መንገድ ማስተማር መንፈሳዊ ስልጣንና የልጅነት መብት ነው፡፡ የእግዚአብሔር ቤትና ሕዝቡ አደራ የተሰጠን ለእኛም ነውና እውነትን መናገር ትክክለኛ መልዕክተኛነት ሲያልፍም ነብይነት ነው፡፡ እውነትን በፍቅር መናገር መሸፋፈን አይደለም፡፡ እውነትን በፍቅር መናገር ስህተትን በጀርባ ከማውራት የአደባባዩን በአደባባይ የግልን በግል መናገር ነው፡፡

 

የአደባባይን በአደባባይ የሚናገርን ሰው የሚወቅሱ ሰዎች ለአደባባይ ስህተት ተባባሪ ናቸው፡፡ መለያቸው የአደባባይ ነገር ሲነካ መቆጣታቸው ነው፡፡

  

የተሳሳተ መመዘኛ

 

ቅን ሰዎች ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በተነሱ "ነቢያት" ጉዳይ ላይ ለሚነሳ ክርክር ‹‹ሰው ሲነሳ አንወድም፣ ሰው እያጠፋ ነው የሚያድገው፣ ልጆች ስለሆኑ እንታገሳቸው… ቅናት ነው፣ እንደ እነርሱ አገልግሉና አሳዩን ወዘተ›› ይላሉ፡፡

 

"ሰው ሲነሳ አንወድም" የሚለውን አባባል ከብዙዎች እሰማለሁ ግን አንድ ጥያቄ አለኝ መጽሐፍ ቅዱስ ሲናገር ልዩ ልዩ አይነት ስጦታ ያላቸው ሰዎች ለቤተ ክርስቲያን መሰጠት የጀመሩት በቅርብ ነው እንዴ? ቀድሞም የተነሱ ሰዎች አሉ፤ ደግሞስ ስህተት ጎልቶ ሲታይ ስህተትን ማረም ሰው ሲነሳ አለመውደድ ነው እንዴ? መርምሩ፣ ፈትኑ፣ ተጠንቀቁ፣ አስጠንቅቁ፣ አልተባልንም?

 

ቅናት ለተባለው ቅናት የሚያስቸግረው ሰው አንድ ከሌሎች በልጦ ለመገኘት የሚፈልግ፣ ትርፍ በሚያስገኝ ጉዳይ ያልተሳተፈ ወይም መንገድ ያጣ፣ ብለን ብንመድበው ታድያ በሁለቱ መመዘኛ እንኳን የሳኦል አይነት ልብ ካልመጣብንና ዘንድሮ እየታየ ያለው ጉዳይ የመወደድና ያለመወደድ የመነገድና ያለመነገድ ካልሆነ በቀር ከሚያስከፍለው ዋጋ አንጻር ነቢይነት ምኑ ያስቀናል? ከቀደሙት ነቢያት እስከ መጥምቁ ዮሐንስ ነቢይነት ምኑ ያስቀናል? ሀቀኛ ነቢይነት አያስቀናም? ከነቢያት ሁሉ የተናገረውን በዓይኑ ያየ ነቢዩ ኤርሚያስ ነው፡፡ ምኑ ያስቀናል? (ትንቢተ ኤርሚያስን ያንብቡ)

 

‹‹ሰው እያጠፋ ነው የሚያድገው›› ስንልስ ሰው ማጥፋቱን እያወቀ ተመለስ አጥፍተሀል የሚሉትን በግድያ ሳይቀር እያስፈራራ ለማደግ እያጠፋ ነው ወይስ አጥፍቶ ጠፊ እየሆነ ነው?

 

ደግሞስ ሰው እያጠፋ ነው የሚያድገው የሚለው መርህ የማን መርህ ነው? መጽሐፍ ቅዱስ በተለይ በትንቢት አገልግሎት ጉዳይ ላይ "እግዚአብሔር ብሏል" እያሉ እየዋሹና እየሳቱ ማገልገልን መማሪያ አላደረገውም፡፡ አያደርገውምም፡፡ "እግዚአብሔር የሚናገረኝ ነብይ ነኝ" ብለን አምነን ሳለን ስንሳሳት ‹‹ተሳስተሀል›› ስንባል የአደባባዩን በአደባባይ የግሉን በግል ለመናዘዝ ካልፈቀድን በሐሰተኛ ነቢይ ላይ የሚመጣው ፍርድ ሁሉ እንደሚከተለን ማወቅ ግድ ነው፡፡

 

ስለ አንዲት ሴት ማርገዝ ጌታ ተናግሮን የልጁን ጾታ ከእኛ መጨመር ተገቢ አይደለም፡፡ የሚሞተውን ሰው ይኖራል የሚኖረውን ይሞታል እያልን፤ አንድ ከእግዚአብሔር አንድ ከኪስ እየተናገሩ እድሜ ዘመንን "መሳሳት ያለ ነው" ማለት አደጋው ትልቅ ነው፡፡ ብዙዎች ከአንድ ትክክለኛ መልዕክት ቀጥሎ ባለ የተሳሳተ ምዕክት ሕይወታቸው ለዘላለም ሊበላሽ ይችላል፡፡

 

‹‹ሚስተር ኤክስ ማን ነው?›› ተብለው ከተጠየቁና በትክለኛው ስም ጥሪ መልዕክት በኋላ "ውጭ አገር በቀጣዩ ወር ትሄዳላችሁ!" ተብለው የማያገኙአቸውን ውድ የስራ እቃዎች በርካሽ ሸጠው ጉዳዩ አልሆን ሲል መልሰው እነዚያን ዕቃዎች በውድ እየገዙና እንደገና እየተደራጁ ያሉ ቤተሰቦችን አውቃለሁ፡፡ እንዲህ አይነቱን ቤት ይቁጠረው፤ ታድያ ልምምዱ በማን ቤተሰብ ላይ ይወሰን? አንባቢ ባንተ ላይ ቢለማመዱ ትፈቅዳለህ? መጽሐፍ ቅዱሳዊስ ነው?

 

እያጠፉ ማደግ አንድ ሌላ ነገር ነው ብንል እንኳን፤ ታድያ "አድጌያለሁ፣ ተቀብቻለሁ፣ ልዩ ቅባት ወድቆብኛል፣ አስደናቂ የትንቢት አገልግሎት፣ የመጠቀ መገለጥ" ወዘተ እየተባለ "ብቁ ነኝ" ብሎ የግል ቴሌቭዥን መክፈት  ድረስ ደርሶ አልፎም ቤተ ክርስቲያን ጀምሮ ማጥፋቱን የሚቀጥል አገልግሎት እያደገ ያለ ሰው ምልክት ነው? ወይስ የአጥፊ? ሳያድጉ መውጣትና አድጎ መውጣት በራሱ ይለያያል፡፡ በአደባባይ በእግዚአብሔር ስም ትልልቅ ውሸት እየተዋሸ ይደጉ ተዋቸው የሚለው አስፈሪ ምክር ነው፡፡ ይልቅ አንድ አስፈሪ ቃል ያስታውሳል፡፡

 

‹‹ተዉአቸው፤ እስከ መከር ጊዜ አብረው ይደጉ፤ በመከር ጊዜም አጫጆችን። እንክርዳዱን አስቀድማችሁ ልቀሙ በእሳትም ለማቃጠል በየነዶው እሰሩ፥ ስንዴውን ግን በጎተራዬ ክተቱ እላለሁ አለ።›› ማቴዎስ 13፡30

 

"እንደ እነርሱ ሆናችሁ አሳዩን" የሚሉ ሰዎች ደግሞ በጣም አሳፋሪ ሰዎች ናቸው፡፡ የጸጋ ስጦታ ልዩ ልዩ ነው፣ የሚበልጥ የጸጋ ስጦታ የለም፡፡ የሚገርመው እንደውም ትንቢት መናገርን ሁላችንም ፈልጉ ተብለናል ትንቢት መናገር ነቢይነትን አይጠይቅም፡፡ ነቢይ የሚባለውን ስምና የአገልግሎቱን ሁናቴ ሰዎች ሁሉ በብርቱ የሚፈልጉት ነገን እንነግራችኋለን ስለሚሉ ነው፡፡ ነገን መስማት የብዙዎቻችን ፍላጎት ስለሆነ፡፡ ታድያ ባልተሰጠው ወይም ዘንድሮ በብዙዎች እንደሚታየው የመሙከራና የግምት አገልግሎት እንሳተፍ? የአንድን ዘማሪ፣ ሰባኪ፣ መጋቢ ወዘተ አገልግሎት አካሄድ ለማረም መነሳት የግድ እንደርሱ ስላልሆንክ ነው፣ ሆነህ አሳየኝ ያስብላል? እስኪ "ሆነህ አሳየኝ?" የምትል አንተም ሆነህ ተቃወም?፡፡

 

የአንድ ሐኪምን ወይም ሾፌርን ያልተገባ አሰራር ለማረምና ለመቃወም የግድ ሾፌርም ሐኪምም መሆን አያስፈልግም፡፡ የሚያስፈልገው የትክክለኛውን አካሄድ መመሪያ ማወቅ ነው፡፡ የእግዚአብሔር ቃል በሙላት ካለን እንደ ቃሉ ያልሆነን አካሄድ ሁሉ ለመቃወምና ለማረም መብቱም ብቃቱም አለን፡፡

 

ድምጽ ለመስማት በግ መሆን በቂ ነው፡፡ በውስጣችን የምሰማውን የመንፈስ ቅዱስ ድምጽ ስለማናምንና ልዩ ልዩ መገለጥ ያመጣን ሰው "የተሻለ ይሰማልኛል" ብለን ስለደመደምን እንጂ ጉዳዩ የቤተ ክርስቲያን መጥቀሚያ ጸጋ ነው፡፡

 

ደግሞስ ስህተት አለ ብሎ የሚያስጠነቅቅ ሰው ነብይ ላለመሆኑ ምን ማስረጃ አለን? እኔ ይህንን ስጽፍ ነቢይ ብሆንስ ነቢይ ለመባል የግድ ስምና ድንኳን የሞላ ሰው ያስፈልጋል? ነቢይነት መመዘኛው ከባድ ነው! እንደውም ነቢይነት በመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ ጋርድ እስኪያስፈልግ የተወደደበት ቦታ አይታይም ማስታወቂያም የለውም፡፡ ነቢዩ ኤልሳዕ እኛጋ መጥቶ ይፈወስ ብሎ ጀኔራል ንዕማንን እንኳ ቢፈውስ በመልዕክት እንጂ ለማስታወቂያ የሰው ዓይን እስኪታክት አልተጠቀመበትም ብርና ወርቁንም አልተቀበለውም፡፡ (2ኛ ነገስት 5)

 

እግዚአብሔር ያላለውን ማለት ቀላል ነውን?

 

‹‹እጄም ከንቱ ራእይን በሚያዩ፥ በውሸትም በሚያምዋርቱ ነቢያት ላይ ትሆናለች እነርሱም በሕዝቤ ማኅበር ውስጥ አይገኙም፥ በእስራኤልም ቤት መጽሐፍ አይጻፉም፥ ወደ እስራኤልም ምድር አይገቡም እኔም ጌታ እግዚአብሔር እንደ ሆንሁ ያውቃሉ።›› ሕዝቅኤል 13፡9

 

በውል በማላስታውሰው አንድ ከተማ ለአገልግሎት ሄጄ በድንገት በነበያት አገልግሎት ዙሪያ ውይይት አዘል ክርክር ተነሳ፡፡

 

ጉዳዩ "በዘመናችን ነቢያት" ጉዳይም ጭምር ሆኖ ነቢይ ይሳሳታል? ሲሳሳትስ ንስሀ መግባት የለበትም? ትንቢት በሰው ፈቃድ ይመጣል? አንድ ነቢይ ቤተ ክርስቲያን መምራት ይችላል? የነቢያት መመዘኛ ምንድነው? ትንቢት በእግዚአብሔር ቃል እንዴት ሊመረመር ይችላል? የነቢያት አገልግሎት መመዘኛና መለኪያ ምንድነው? የመሳሰሉት ጥያቄዎች በውይይቱ መካከል ተነስተው ነበር፡፡

 

ውይይቱ ስለ ትንቢት ስህተቶች ባቀረብኩት ማስረጃ በተናደዱ "ነቢይ ተቃዋሚ አትሁን! ነቢይ ሊሳሳት ይችላል! እኛ አገር ሰው ሲነሳ አንወድም!" ባሉኝ አንድ የቤተ ክርስቲያን መሪ ቁጣ አዘል ንግግር ተቋረጠ፡፡

 

እኔም ቀጠል አደረኩና ወደተቆጡኝ የቤተ ክርስቲያን መሪ እጆቼን ጠቁሜ እንዲህ አልኩ፡-

 

‹‹ትናንት አሁን የተቃወሙኝ እኚህ ሰው ቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ ያሉት ሽማግሌዎች እንዳልተመቿቸው፣ ሽማግሌዎቹ አስቸጋሪ እንደሆኑ ስለዚህም ቤተ ክርስቲያኗን ለቀው መሄድ እንደፈለጉም ነግረውኛል›› አልኩኝ፡፡

 

ሽማግሌዎች ደነገጡ፤ መሪውም ፊታቸው ተለዋወጠና

 

‹‹የት ቦታ ነው እንዲህ ያልኩት?›› ብለው አፈጠጡብኝ፡፡ እኔም ዝም አልኩና ቁጣቸው ጨመር ሲያደርግ መልሼ

 

‹‹ይኸውላችሁ እኔ እርሳቸው ያላሉትን ለእናንተ በመናገሬ መሪያችሁ ተቆጡ! ምክንያቱም ያላሉትን ነው ያልኩት! እግዚአብሔር ያላለውን ሰዎች ሲናገሩ ጉዳዩ ትክክል አይደለም ይህ ትንቢት ስህተት ነው ሲባል እንቆጣለን የእኛ ስም በሐሰት ወሬ ሲነሳ ነብር እንሆናለን እግዚአብሔር ያላለውንና ሊል የማይችለውን ማለትም ከቃሉ የተፋታ ትንቢት እንኳ እየሰማን ዝም እንላለን ምክንያቱም ከእግዚአብሔር ስም ይልቅ ስማችን በልጦ፣ ከማንም ላለመጣላት፣ ተቃዋሚ ላለመባል፣ ጥቅማ ጥቅም ላለማጣት፣ ሕዝብን ደስ ለማሰኘት፡፡›› አልኳቸው፡፡ ከዚያ በኋላ ሁሉም ዝም አለ፡፡ እስኪ ያላላችሁትን አላችሁ ሲባል በራሳችሁ አስቡት? እስኪ ጎበዝ ከሆናችሁ መንግስት ያላላውን በሉ? እግዚአብሔር ተሟጋች የሌለው፣ በስሙ ሲነገድ የሚናገርለት የሌለው መሰላችሁ? አለው፡፡ እውነተኞች ነቢያት አሉት፡፡ ቆራጥ ልጆች አሉት፡፡ አንተስ አንባቢ ከማን ወገን ነህ?

 

‹‹እነሆ፥ ሐሰትን በሚያልሙ በሚናገሩም በሐሰታቸውና በድፍረታቸውም ሕዝቤን በሚያስቱ በነቢያት ላይ ነኝ፥ ይላል እግዚአብሔር እኔም አልላክኋቸውም አላዘዝኋቸውምም ለእነዚህም ሕዝብ በማናቸውም አይረቡአቸውም፥ ይላል እግዚአብሔር፦›› ኤርሚያስ 23፡32

 

ጥቂት የቀጣፊና ውሸተኛ ነቢያት ግልጽ ስህተቶች 

 

በቴሌቭዥን መስኮትም ሆነ በዩቲዩብ ድረገጾች ከበቂ በላይ ማስረጃ ማግኘት የማይቸግርባቸውን መጽሐፍ ቅዱሳዊ ያልሆኑና ሰዎች ከኪሳቸው አውጥተው የሚናገሩአቸውን እግዚአብሔራዊ ያልሆኑ ትንቢቶችን እንደሚከተለው አቀርባለሁ፡፡ ይህ ትንቢት አዘል ንግግር በነቢያት ብቻ ሳይሆን ቃሉን በሚያስተምሩ አንዳንድ ሰባኪዎች ዘንድም የተለመደ ንግግር ነው፡፡ የሚገርመው ግን ነቢያት ነን ብለው ያመኑ ሰዎች በሙሉ ስልጣንና በኩራት "እግዚአብሔር ምስክሬ ነው" በሚል የቅጥፈት ምሽግ ውስጥ ሆነው መናገራቸው ነው፡፡ ከታች የማቀርባቸው ሦስት አራት የሚሆኑ ግልጽ የውሸት ትንቢቶች ብዙውን ለመመርመር መነሻ እንዲሆኑ ነው፡፡

 

እነሆ፥ ከምላሳቸው ትንቢትን አውጥተው። እርሱ ይላል በሚሉ ነቢያት ላይ ነኝ፥ ይላል እግዚአብሔር፦ ኤርሚያስ 23፡31

 

  1. "የጌታ መንፈስ ከዚህ ጉባኤ መካከል ምድሪቱ የማትችላቸው፣ አጋንንት ፊታቸው የማይቆም፣ የተናገሩት ሁሉ የሚሆንላቸው ወዘተ አስገራሚ ሰዎችን አሁን እቀባለሁ ብሎኛል" እኔ ነኝ የሚል ዘሎ ይቀበል፡፡

 

ይህ አይነቱ ቀጣፊና ስጋዊ ትንቢት ሲነገር አሜን ብሎ የሚንቀጠቀጠውንና ለመውሰድ የሚዘለውን ሕዝብ ስንመለከት ምን ያህል የእግዚአብሔር ቃል እንደሌለው አልፎም በነቢይ ተብዬዎች አንደበት የተነገረ ሁሉ እንደሚሆንለት ያመነ ሚስኪን ሕዝብ እንደበዛ ማወቅ ቀላል ነው፡፡

 

የሚገርመው የመሪዎች ዝምታና አብሮ መዝለልና ድጋፍ መስጠት ነው፡፡

 

በመጀመሪያ ምድሪቱ የማትችላቸው፣ አጋንንት ፊታቸው የማይቆም፣ የተናገሩት ሁሉ የሚሆንላቸው እነማን ናቸው? መጽሐፍ ቅዱስ እነዚህ ይነሳሉ ብሏል ወይ? አጋንንት ፊቱ የማይቆም ሰው ተነስቶስ ያውቃል ወይ?

 

ደግሞስ አይሆንም እንጂ እንደዚህ ያሉ ሰዎችንስ እግዚአብሔር አስነሳለሁ ካለ በሻሞ ነው እንዴ? ዘሎ አሜን በማለት እንዲህ ያለ ነገር ይሆንልሀል ከየት የመጣ መርህ ነው? ወደ ውኃው ዘሎ የገባ ይፈወሳልን ለመጥቀስ ነው? አይቻልም ያ ሌላ ይሄ ሌላ፡፡

 

እግዚአብሔር ለጠራኋቸው ስራ ለዩልኝ ይላል እንጂ በሻሞና ዘሎ በመውሰድ የሰርግ ከረሜላ ጨዋታ በምንም መልኩ ጤና አይደለም፡፡ እንግዲህ አውራ ነብይ ነኝ የሚሉት ይህንን ሕዝብ በየቦታው የሚያንገላቱትና ሲያዘልሉት የሚውሉት በእንዲህ ያለ ከቃሉ በተፋታ መገለጥ መሳይ ውሸት ነው፡፡ እነርሱ ቆሙ ማለት ነገር ሁሉ ተቀየረ ማለት ነው? ሀይ የሚል ስለሌለ እንጂ ነቢይ የሚናገረውን ሌሎች ይመርምሩ ይለዩአቸውም ተብሏል፡፡

 

‹‹ነቢያትም ሁለት ወይም ሦስት ሆነው ይናገሩ ሌሎችም ይለዩአቸው፤›› 1ኛ ቆሮንቶስ 14፡29

 

ትንቢት በእግዚአብሔር ቃል የሚመዘን ከሆነ አጋንንት ፊቱ የማይቆም ሰው እስከዛሬ አልተነሳም ወደፊትም አይነሳም፡፡ የሚገርመው በአብዛኛዎቻችን ጉባኤ አጋንንት የሚወጣው እራሱ በጋራ በሆነ ረጅምና አሰልቺ ጸሎት ከሆነ ቆይቷል፡፡ እየዞሩ በየፕሮግራም ቦታው ከሚጮሁት ውጭ፤ ደግሞም ማስጮህና መስወጣት ተቀላቅሎብናል ይህም ትልቁ የቤት ስራችን ነው፡፡

 

  1. "ጌታ ተናግሮኛል ከዚህ ቀን ጀምሮ መከራችሁን፣ ችግራችሁን፣ ድህነታችሁን አታዩትም"

 

እግዚአብሔር በዘመናት መካከል የሚናገር አምላክ ነው፡፡ አሜን፡፡ እግዚአብሔር ተናገረ ማለት ተናገረ ነው፡፡ በዚህ ከተስማማን በአንድ ጉባኤ መካከል ወይም ብዙ ሺህ ህዝብ ባለበት፣ አልፎም በከተማ ደረጃ ሲናገር በትክክለኛ ነቢያት የተነገሩ መልዕክቶች ተፈጻሚ ይሖናሉ፡፡

 

‹‹….ውኃው ወዳለበቱም ምንጭ ወጥቶ ጨው ጣለበትና። እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ይህን ውኃ ፈውሼዋለሁ ከዚህም በኋላ ሞትና ጭንገፋ አይሆንበትም አለ። ኤልሳዕም እንደ ተናገረው ነገር ውኃው እስከ ዛሬ ድረስ ተፈውሶአል።›› 1ኛ ነገስት 2፡21-22

 

ነቢይነትና ትንቢት እንዲህ ነው፡፡ ነቢይ ነኝ ብለው በሚያምኑና ራሳቸውን በተለያየ ቅጥያ ስም የሚጠሩ በርካቶች በእግዚአብሔር ብሎኛል ካባ መከራህ፣ ድህነትህ፣ ጭንቀትህ፣ መራራው ነገርህ ወዘተ ከዛሬ ጀምሮ አታየውም ተመቷል! ብሎ መናገርን ልማዳቸውና መብታቸው አድርገው ስለመንቀሳቀሳቸው አሁን ከቴሌቭዥናቸውና ከድረገጻቸው ማግኘት አይቸግርም፡፡

 

ጥያቄው እግዚአብሔር ብሏል ወይ ነው? ካላለ ሐሰተኛነትን ማመንና መቀበል አማራጭ የለውም፡፡ በዕምነት ትንቢት መናገር አንድ ሌላ ነገር ነው፤ ጌታ ብሎኛል ሌላ ነገር ነው፡፡ ትንቢትን በእግዚአብሔር ስም መናገር ታላቅ አደጋና ቅጣቱ ከባድ ነው፡፡ ስለዚህ ነቢያቶቻችን የእግዚአብሔር ነቢያት ናቸው? ወይስ አንዴ ጌታ ይጠቀምባቸዋል አንዳንዴ ደግሞ ሰይጣን? ወይም ስጋቸው? የሚናገሩትስ ከእግዚአብሔር ለመሆኑ ቃሉ ከጣላቸው ምን ልናደርግ ይገባል? እንዳይታረሙ አለቃና ቤተ ክርስቲያን የላቸውም፡፡ ነቢያት በቤተ ክርስቲያን ስር መሆን የሚገባቸው አንዱ ለዚህ ነው፡፡ አሁን ግን መመርመርና መለየት አይቻልም፡፡

 

ታድያ በየቴሌቭዥኑ መስኮት "እግዚአብሔር ብሎኛል" እየተባለ የሚለቀቀው ጅምላ የሐሰት ትንቢት ከማን መጣ?

 

በመሰረቱ ጭንቀት፣ ድህነት፣ መከራ በራሳቸው ካልተተነተኑ በጅምላ ንግርት አገርንም ምድርንም ግለሰብንም አይለቁም፡፡ አንድ ሰው ነቢይ ስለሆነ በግሉ  ልተንብይ፣ ልበል፣ እያለ የሚወስናቸው ጉዳዮችም የሉም፡፡ ቢኖሩ ኖሮ በትንቢት የሚሰጡንን የገንዘብ ተስፋ ብዙዎቹ ለራሳቸው ያዞሩት ነበር፡፡ ግን ለእኛ የትባረካለህ ትንቢት ነግረውን ብራችንን ይወስዱብናል፡፡ ለራስ የማይተርፍ ትንቢት፡፡ ኤልያስ የመበለቱዋን ምግብ በልቶ ትቷት አልሄደም ሦስት ዓመት ተባረከች ረሀቡንም አለፈች፡፡ የቀድሞ ነቢያት እንዲህ ነበሩ፡፡

 

  1. ጌታ በዚህ ከተማ ላይ ከዚህ ቀን ጀምሮ ከተማይቱን በወንጌል የሚገለባብጡ ይነሳሉ ብሎኛል

 

ከዚህ ቀን ጀምሮ ብሎ እግዚአብሔር የተናገረባቸው ጉዳዮች ሁሉ ያለ ምንም ማመቻመች የሚፈጸሙት ከዚህ ቀን ጀምሮ ነው፡፡

 

በዘመናችን በቤተ ክርስቲያን እንዲህ አይነት ቅጥፈት አዘል ትንቢት "ከጎንህ ላለው እንዲህ በለው ጌታ እንዲህ ይልሀል" እየተባለ ከሚነገረው ጀምሮ እግዚአብሔርን የቆሎ ጓደኛ በማድረጋችን የምንጠየቅበት ትልቅ አመጻችን ነው

 

"ከጎንህ ያለውን ጌታ በታላቅ ቅባት አስነስቸሀሉ፣ ከጎንህ ያለውን ጌታ ትዳርህን ባርኬያለሁ ይልሀል (ያገባውንም ያላገባውንም)፣ ከፊትህ ክብር አለ ይልሀል ጌታ" (ከፊቱ ቀብር ያለውን ጭምር) እየተባለ በእግዚአብሔር ስም የሚነገር ደፋር የኪስ ትንቢት ለሀሰተኞች እንደ አሸን መፍላት ቢዳርገን ምን ይገርማል?

 

በቀጣይ

 

ነቢያት ቤተ ክርስቲያን ይመራሉን? ብዙዎች በግላቸው ለምን ተሰማሩ?.... የሚለውን እንመለከታለን በቸር ይግጠመን፡፡

                          

 

[1] ዴቪድ ፔትስ፤ ትርጉም እንዳለ ገ/መስቀል፤ የአካሉ ገንቢዎች ገጽ 49-50 (ፔንቴኮስታል ቲዎሎጂካል ኮሌጅ፤ 2000 ዓ.ም) ገጽ 49-50

Read 24221 times Last modified on Tuesday, 19 July 2016 01:25
Dereje Mulatu

ደረጀ ሙላቱ ዘማሪ፣ ሰባኪ፣ ጸሐፊና ገጣሚ ሲሆን ከባለቤቱ ከሲስተር አዜብ ስዩምና ከልጆቹ ከፍቅር ደረጀና ከኢዩ ደረጀ ጋር በኢትዮጵያ ይኖራል።

Email This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it.

Nahu's Corner

 

 

 

.

Right Now

We have 102 guests and no members online

About Us

Semayawi Thought is an online magazine published in Amharic and English, focused on contents to spiritual and personal growth.