You are here: HomeOpinionsመሪነት የሩቅ ጥቆማ አይደለም

መሪነት የሩቅ ጥቆማ አይደለም

Written by  Monday, 11 January 2016 09:48

ብዙ ጣጣ ቢኖርበት ''ምን አባቱ " ብለን መተው ከማንችላቸው የሕይወት ጉዳዮች አንዱ መሪነት ነው:: የምናተኩርበት አውድ ቤተ ክርስቲያን ይሁን ወይም ቤተሰብ : አገር ይሁን መንደር መሪነት በጥሞና መታሰብ ያለበት ጉዳይ ነው :: ስለ መሪነት ሳስብ ከማስታውሳቸው ንባቦች አንድ መንደርደሪያ ልውሰድ : ቻርልስ ሲምፕሰን የተባሉ የቤተክርስቲያን መሪ ገጠመኝ ነው ::

 

"መኪና ተከራይቼ ወደ ሎሳንጀለስ አየር ማረፊያ የነዳሁበት ያ ቀን ትዝ ይለኛል::ከዚህ በፊት መንገደኛ ሆኜ ባውቀውም መኪና እየነዳሁ ለመሄድ ግን የመጀመሪያ ጊዜዬ ነበር ::ባለ ስድስት መስመር ፈጣን አውራ ጎዳና ውስጥ ገብቼ ሳሽከረክር ባለቤቴ የከተማውን ካርታ ይዛ ትረዳኝ ነበር:: ብዙ ከሄድን በኋላ ነው ራሱን ሎሳንጀለስን አልፌ እንደወጣሁ ያወቅሁት::

 

ምንም አይደል በቂ ጊዜ አለ አልኩና ከዋናው መንገድ ፈቀቅ ብዬ ቀይ መብራት ያቆመውን ነጂ ' ወደ አየር ማረፊያው የምደርሰው እንዴት ነው?' ብዬ ጠየቅሁ::'ወደ ኋላ ዙርና ወደ ደቡብ ሂድ ; የሚቀጥለውን ዋና ጎዳና በቀኝ በኩል ያዝና ብዙ ኪሎ ሜትር ወደ ፊት ሂድ : አታጣውም አለኝ::

 

ዞረን ወደ ደቡብ ሄድን : የሚቀጥለውን ቀኝ ያዝንና ብዙ ነዳን : ግን ኤርፖርቱ የለም :: ቀኑ እየመሸ መጣ : ጊዜም እያነሰ ነው::'ምን አልባት አውሮፕላኖቹ የሚበሩበት አቅጣጫ ይመራኝ ይሆን?' ብዬ አሰብኩ : ግን እርሱም አልሰራም::

 

ከዋናው መንገድ እንደገና ወጣሁና 'የቤንዚን ማደያው ሰራተኛ ሊረዳኝ ይችላል' ብዬ ወደ ማደያው መኪናዬን አስጠጋሁ : ቦታው ጨለምለም ብሎአል ::

 

እባክዎ ሊረዱኝ.....?

 

እኔ እንግሊዝኛ ስናገር እርሱ በስፓኒሽ ይመልስለኝ ጀመር::

 

ሌላ የሚረዳኝ.........?

 

ምንም መግባባት አልተቻለም : ስፓኒሾች ሰፈር ነበር የገባነው ::ቦታው እንደጠፋኝ በደምብ ገባኝ ::በልቤ 'ምነው የማውቀው ባይመስለኝ ኖሮ' አልኩና አንድ መንገድ ላይ ስንወጣ መብራት አቆመን::

'እባክዎን ወደ ሎሳንጀለስ አየር ማረፊያ እንዴት እንደምንደርስ ሊነግሩኝ ይችላሉ?' አልኩና አጠገቤ የነበረውን ሌላ አሽከርካሪ ጠየቅሁ::

 

'ተከተለኝ ' አለኝና እንደረፈደብኝ ያወቀ ይመስል ይከንፍ ጀመር::


ሰውየውን አላውቀውም : መንገዱን ማወቁንስ በምን አውቃለሁ? አንድ ነገር ግን እርግጥ ነበረ : መንገዱን እኔ አለማወቄ:: እሱ ወደቀኝ ሲዞር እኔም ወደቀኝ: ወደግራ ሲዞር እኔም ወደግራ : ቢጫ መብራት ሲጥስ እኔ ቀይ እየጣስሁ ሲያፈጥን እያፈጠንሁ የ እርሱን ጅራት ብቻ እንደተከተልሁ ከ አስር ደቂቃ ግስገሳ በሁዋላ የሎስ አንጀለስ አየር ማረፊያ ላይ ከቸች ስንል መንግስተ ሰማይ የገባሁ ነው የመሰለኝ:: ምስጋናዬን በታላቅ ፈገግታ ገልጬ ተሰናበትኩትና ወደ አውሮፕላኑ አመራሁ:ለጥቂት ሳይዘጋ ደረስሁ::

 

መሪነት ምን እንደሆነ የገባኝ ያን ቀን ነው :: መሪነት የሩቅ ጥቆማ አይደለም:መሪነት ማመላከት አይደለም: መሪነት ወደሚፈለገው ግብ ራስ ሔዶ ማሳየት ነው ::

 

ይህን ያሉት ቻርለስ ሲምፕሰን ናቸው :: የ እርሳቸውን እዚህ ላይ እንግታና ወደ እኛ ወደ ሃገራችን ወደ ቤተክርስቲያናችን እንመልከት::

 

እኛ መሪዎች አሉን ወይ? ዛሬ በቤታችን ውስጥ : በቤተክርስቲያን : በአገር ደረጃ: በህብረተሰብ መካከል የሚሄዱበትን የሚያውቁ: ወደ ርግጠኛ ግብ የሚገሰግሱ : ይዘው የሚያደርሱን መሪዎች አሉን? እኔ እንጃ! እኔ እንጃ! እኔ እንጃ!

 

በየቦታው: በየመደቡ : "መሪዎች" መሾማቸው : በየስብሰባው "መሪዎች" መምረጣችን : ማሰልጠናችንና መሰየማችን አልቀረም :: ይህ ሁሉ ግን እርግጠኛ መሪዎች እንዳሉ ማስተማመኛ የሚሆን አይመስለኝም ::ምናልባት እያፈራን ያለነው ''ነገር አርቃቂዎች" ; "ካርታ ነዳፊዎች ብቻ" : " እስከጊዜው ይዤ ልቆይ ተግደርዳሪዎች " : "ኢላማቢስ ተኩአሾች" ወዘተርፈ... ቢሆንስ?ገና በበቂ ያልተመለሰ የመሪነት ጥያቄ አለ : በቤተ ክርስቲያንና ከዚያም ውጭ የ እውነተኛ መሪ ጥማት ሕዝቡን እንዳንገበገበ ነው : ብዙ አይኖች ይንከራተታሉ : "ኑ በዚህ" የሚላቸው ሰው ፍለጋ :: የማን አይኖች? የወጣቶች : የሽማግሌዎች : የሴቶች : የሰባኪዎች; የዘማሪዎች : የነጋዴዎች : የተማሪዎች ...:: ዛሬ ገብተው የሚያስገቡ መሪዎች እንዲበዙልንና በዚህ አገልግሎትም ውስጥ ካለን ገብተን የምናስገባ እንድንሆን ጸሎትና እርምጃ እንጀምር!

Read 12212 times Last modified on Monday, 11 January 2016 13:09
Negussie Bulcha

Website: www.negussiebulcha.com Email This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it.

Nahu's Corner

 

 

 

.

Right Now

We have 309 guests and no members online

About Us

Semayawi Thought is an online magazine published in Amharic and English, focused on contents to spiritual and personal growth.