You are here: HomeTheologyመስቀሉን ማኮሰስ፣ ስቁሉን ማራከስ

መስቀሉን ማኮሰስ፣ ስቁሉን ማራከስ

Written by  Thursday, 01 December 2016 03:43

የክርስትና እምነት ሁለት እውነቶችን ያስተምረናል፤ በሰዎች ሊታወቅ የሚችል አምላክ መኖሩ የመጀመሪያው ሲሆን፣ በእግዚአብሔር ፊት ብቁ እንዳይሆኑ የሚያደርጋቸው ብልሽት (ውድቀት) በሰዎች ዘንድ መኖሩ ደግሞ ሁለተኛው ነው። የሰውን ውድቀት ሳይገነዘቡ እግዚአብሔርን ማወቅ፣ ወደ ትዕቢት ይመራል፤ እግዚአብሔርን ሳያውቁ የሰውን ውድቀት ማወቅ ደግሞ ወደ ተስፋ ቢስነት ይመራል። ኢየሱስ ክርስቶስን ማወቅ ግን ሁለቱንም በአንድ ጊዜ ወደ መረዳት ያደርሳል።[1] ይህም ነገረ ክርስቶስን (የክርስቶስን ማንነት እና ሥራ) የክርስትና ልብ፣ የክርስቲያናዊ አስተምህሮዎች ሁሉ እምብርት ያደርገዋል። ስለዚህም “ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ያለን መረዳት ክርስትናችን ትክክለኛ መሆን አለመሆኑ የሚፈተሽበት ነው። ማንነቱን ወይም ለምን እንደ መጣ ወይም ለእኛ ምን እንደ ፈጸመ በመሠረታዊ መንገድ ከሳትን፣ በ‘ሌላ ኢየሱስ’ እና በ‘ልዩ ወንጌል’ ወጥመድ ውስጥ ወድቀናል ማለት ነው (2ቆሮ. 11፥4፤ ገላ. 1፥6-9)።”[2] በአጭሩ ለማስቀመጥ፣ ነገረ ክርስቶስ ከመሠረቱም የክርስትና ዐልፋ እና ዖሜጋ ነው!

 

ስለ ነገረ ክርስቶስ ሲነሣ ደግሞ ነገረ መስቀሉ ዋነኛ ይሆናል፤ ምክንያቱም መስቀሉ የኢየሱስ ሕይወት ማዕከል፣ የምድር ሕይወቱ መካከለኛ ጕዳይ፣ የአገልግሎቱ እምብርት ነውና! አራቱንም ወንጌላት ስናነብ አንዱ ብቻ ነው ስለ እርሱ ውልደትና ልጅነት የሚያትተው። ከዚያ ውጭ ግን አብዛኞቹ ከሠራቸው ተአምራት እና ከሰጣቸው ትምህርቶችም በላይ የሚያተኵሩት ወደ መስቀሉ በሚያመሩ ሁነቶች ላይ ነው። ይህንን በአግባቡ እንግለጠው ከተባለ፣ መስቀሉ የአዲሱ ኪዳን ዋና ጭብጥ ነው።[3] ስለዚህም ነገረ መስቀል የነገረ ክርስቶስ ማዕከል መሆኑን መረዳት ግድ ይሆናል።

 

መስቀሉ የታሪክ ማዕከልም ነው፤ እኛ ክርስቶስ የዛሬ ሁለት ሺህ ዓመት በመስቀል ላይ ወደ ፈጸመው መሥዋዕትነት ዛሬ መለስ ብለን እንደምንመለከት፣ ከክርስቶስ በፊት የነበሩ ሰዎችም እርሱ ስለ እነርሱ በመስቀል ወደ ፈጸመው መሥዋዕትነት ፊታቸውን አቅንተው ይመለከታሉ።[4] መስቀሉ ከሌለ፣ ክርስትና የለም በማለት ይህንን በቀላሉ መግለጥ ይቻላል። እናም መስቀሉ የእምነታችን (የሃይማኖታችን) ማዕከል ካልሆነ፣ ሃይማኖታችን ኢየሱሳዊ ሃይማኖት አይደለም።[5] “እግዚአብሔር የታወቀውም ሆነ መልካም ሐሳቡ የተፈጸመው በክርስቶስ መስቀልና ትንሣኤ ነውና እግዚአብሔርን የምናውቀው የተሰቀለውንና ከሙታን የተነሣውን (ስቁሉንና ንሡኡን) ኢየሱስ ስናውቅ ነው።[6] ስለዚህም የእያንዳንዱ አማኝ (የሥጋ ለባሽ ሁሉ ማለትም ይቻላል) ተቀዳሚ ሥራ እግዚአብሔርን በክርስቶስ ለማወቅ መማር ይሆናል።[7]  

 

  1. መስቀሉን የሚያራክሱ፣ ኢየሱስን የሚያኮስሱ

የሚያሳዝነው ግን፣ የተሰቀለውን (ስቁሉን) ኢየሱስ እና የመስቀል ሥራውን የሚያራክሱና የሚያጣጥሉ ባለ ልዩ ልዩ ስም አገልጋዮች በዙሪያችን መኖራቸው ነው። ከእነዚህ መካከል መጋቢ ኤልሻዳይ አበራ፣ ሐዋርያው ዘላለም ጌታቸው፣ መጋቢ ፒተር ማርዲግ እና ኀይሉ ዮሐንስ ይገኙበታል።[8] እነዚህም ሰዎች ኢየሱስ በጌቴሴማኒ ሳለ የማንነት ለውጥ እንደ ተካሄደበት፣ በመስቀል ላይ ወደ ሰይጣንንት እንደ ተቀየረ (እንደ ሰየጠነ)፣ ወደ ኀጢአትነት እንደ ተለወጠ፣ የእግዚአብሔር ልጅነቱ እንደ ተወሰደበት፣ የዘላለም ሞት ወይም መንፈሳዊ ሞት እንደ ሞተ፣ አዲስ ፍጥረት ሆኖ እንደ ተነሣ፣ ዳግመኛ እንደ ተወለደ … ያስተምራሉ።[9] የእነዚህ ትምህርቶች ዋነኛ ችግር፣ ትምህርቶቹ በጠቅላላ መጽሐፍ ቅዱሳዊ አለመሆናቸው ነው። በዚህ ጽሑፍም የእነዚህን ሰዎች ትምህርት በአጭሩ ተመልክተን ከመጽሐፍ ቅዱስ አንጻር እንፈትሻቸዋለን።[10]

 

ይህ ጽሑፍ የዚህ አስተምህሮ አቀንቃኞች የሆኑት መጋቢ ኤልሻዳይ አበራ፣ ሐዋርያው ዘላለም ጌታቸው እና ኀይሉ ዮሐንስ በቅድሚያ እንዲያገኙትና እንዲያነብቡት ተደርጓል። ከእነዚህም መካከል ከኤልሻዳይ አበራ እና ከኀይሉ ዮሐንስ ጋር በኢሜይል ውይይት ቢካሄድም፣ ሐሳባቸው በትክክል እንደ ቀረበ ከመግለጥ ውጭ የአቋም ለውጥ ስላላካሄዱ ይህንን ጽሑፍ ይፋ ማድረግ ግድ ሆኗል።

 

በደቡብ አፍሪካዋ ጆሀንስበርግ ከተማ የምትገኝ ቤተ ክርስቲያን መጋቢ የሆነው ኤልሻዳይ አበራ “የመዋጀታችን እውነታዎች” በሚለው መጽሐፉ፣[11] ሰው ሲፈጠር የእግዚአብሔርን ማንነት የተቀበለ እና የእግዚአብሔርን ብቃት የተካፈለ መሆኑን ከመናገር ይጀምራል (ገጽ 2)።[12] ግና ይህ የመለኮትን ማንነት የተካፈለው ሰው በኀጢአት ወድቆ የሰይጣንን ተፈጥሮ ተካፈለ (ገጽ 5 እና 6)። ኤልሻዳይ እንደሚለው፣ “ሰው ሰይጣን ነው … ምክንያቱም ሰይጣን እጁን ጭኖበታል፤ የሰይጣንን ተፈጥሮ ተካፍሏል” (ገጽ 6)። “ሰውም ኀጢአትን ባደረገበት ቅጽበት ከእግዚአብሔር ሕይወት ወጥቶ የሰይጣንን ተፈጥሮ ስለ ተካፈለ፣ እግዚአብሔር ሰውን ሲያይ የሚያየው ሰይጣንን ነው። … አዳም የሰይጣንን ፈቃድ የፈጸመው ሆን ብሎና ፈቅዶ ነው። ስለዚህ እግዚአብሔር ሰውን ሲያይ የሚያየው ሰይጣንን ነው /በሰይጣን ዐይን ነው/። … ልክ ሰይጣን ከእግዚአብሔር ፊት እንደ ተጣለ [እና] እንደ ወጣ የሰውም ሁኔታ ያው ሆነ” (ገጽ 11)። “ሰው የሰይጣንን ተፈጥሮ ስለ ተካፈለ፣ እግዚአብሔር ከሰው ጋር ኅብረት ማድረግ አልቻለም” (ገጽ 14)። “ሰይጣን በእርግማን ውስጥ ለሰው ያካፈለው የራሱን ተፈጥሮ ነው። … በእግዚአብሔር ደረጃ፣ የእግዚአብሔር መልክና ሕይወት የነበረው ሰው በኀጢአት ከእርግማን በታች ሲሆን የሰይጣንን ደረጃ፣ የሰይጣንን ተፈጥሮ፣ የሰይጣንን ማንነት እና የሰይጣንን ሕይወት ተካፍሎ መኖር ጀመረ። ሰው በኀጢአት ሲወድቅ የእግዚአብሔር ማንነት ከሰው ወጣና የሰይጣን ማንነት ደግሞ ወደ ሰው ገባ” (ገጽ 15)።

 

ኤልሻዳይ አበራ፣ ይህኛው የሰይጣንን ባሕርይ የመካፈል ሁነት፣ የዘላለም ሞት ተብሎ እንደሚጠራ ከተናገረ በኋላ የሰውን ልጅ ለማዳን፣ ኢየሱስም የዘላለም ሞት መሞቱን መናገር ይቀጥላል። ይህንንም ሐሳብ፣ “ክርስቶስ … ለሰዎች የተሰጠውን የዘላለም ቅጣት ተቀጣ …  የዘላለምን ሞት ሞተ” (ገጽ 39)። “ኢየሱስ እኛን ለመዋጀት በእኛ ኀጢአት ምክንያት ልጅነቱን አጥቶ /የዘላለም ሞት ሞቶ እንደ ነበር/ ያስረዳል። … ስለ እኛ ኀጢአት የዘላለምን ሞት ሞቶ በነበረበት ሰዓት” ሲል ያብራራል (ገጽ 46)። በዚህ ሰው አስተምህሮ መሠረት፣ የዘላለም ሞት ማለት፣ “የሰይጣንን ተፈጥሮ መካፈል ማለት ነው። ከሰይጣን ጋር ለዘላለም መኖር ማለት ነው” (ገጽ 16)። ስለዚህም ኢየሱስ የዘላለም ሞት ሞተ ማለት፣ ኢየሱስ የሰይጣንን ተፈጥሮ ተካፈለ ማለት ነው። የሰው ልጅ ከመለኮት ብቃት ተካፋይነት የሰይጣንን ተፈጥሮ ተካፋይ ወደ መሆን እንደ መጣ፣ ጌታ ኢየሱስም ከመለኮት ባሕርይ ተካፋይነት የሰይጣንን ባሕርይ ተካፋይ ወደ መሆን መጣ።

 

ኤልሻዳይ አበራ፣ ገላትያ 3፥13 ስለ ኢየሱስ እርግማን መሆን የሚናገረውን ተመርኩዞ፣ “እርግማን ማለት፡- ለውድቀት፣ ለጥፋት መወሰን ወይም መመደብ ማለት ነው። የሰይጣንን ሕይወት መካፈል ነው” ሲል ብያኔ ያስቀምጣል (ገጽ 81)። አስቀድሞ ደግሞ፣ “ከእርግማን በታች” መሆን፣ “የሰይጣንን ደረጃ፣ የሰይጣንን ተፈጥሮ፣ የሰይጣንን ማንነት እና የሰይጣንን ሕይወት ተካፍሎ መኖር” ማለት መሆኑን ነግሮን ነበር (ገጽ 15)። ስለዚህ ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ እኛ እርግማን ሲሆን፣ የሰይጣንን ሕይወት ተካፍሎ መኖር ጀመረ ማለት ነው። ይህም መሰይጠን ነው።

 

የ“ተልእኮ ለትውልድ” ቤተ ክርስቲያን መሪ የሆነው ሐዋርያው ዘላለም ጌታቸው ደግሞ “ማራናታ” ከተሰኘ መጽሔት ጋር ባደረገው ቃለ ምልልስ፣ ይህንኑ ሐሳብ በሌላ አገላለጽ ያስረዳል።[13] ዘላለም፣ “ኤክሶደስ ቲቪ ሾው” በተባለ ዝግጅት በዚህ ጕዳይ ላይ ጥያቄ ሲቀርብለት፣ “ኢየሱስ ሰየጠነ” በማለት ያስተማሩት ሌሎች እንጂ እርሱ አለመሆኑን አስተባብሎ ነበር። ይህ ቃለ መጠይቅ በተላለፈ በጥቂት ሳምንታት ውስጥ ግን ይህንኑ ሐሳብ በይፋ ማቀንቀን ጀምሯል።

 

ዘላለም፣ “ሰየጠነ” የሚለው ቃል፣ “ሞተ ማለት እንጂ … ሌላ ትርጕም የለውም” ሲል የቃሉን ትርጓሜ በብልጠት ያስቀምጣል፤ ትርጓሜው ከየት እንደ ተገኘ ጥያቄ እንዳይቀርብበትም፣ “‘በምንኛ?’ ብለው ደግሞ የሚሟገቱ ሰዎች ይኖራሉ። በግሪክ፣ በሂብሩ [በዕብራይስጥ] እንድል ነው የሚጠብቁት፤ ግን አይደለም” ሲል አስቀድሞ በር ይዘጋል (ገጽ 8)። ከዚያም “‘ኢየሱስ ለኔ የሞተው’ ስትል በሌላ አማርኛ ‘ለኔ የሰየጠነው’ እያልክ ነው። እንደ ብርቅ የሚወራ ሳይሆን፣ የዕለት ተዕለት ኑሯችን ነው” በማለት ነገሩን ቀለል አድርጎ ሊያቀርብ ይጥራል (ገጽ 11)። ከዚያ ግን አይቀሬው አስተምህሮ ብቅ ማለቱ አልቀረም። “ሰይጣንን ለመሻር ኢየሱስ ሞተ። እርግማንን ለመሻር እርግማን ሆነ፤ ኀጢአትን ለመሻር ኀጢአት ሆነ። በሞት ላይ ሥልጣን ያለውን ለመሻር ሞተ። ሞተ ማለት ያንን ድንበር ዐልፎ ወደ ሰይጣን መንግሥትና ሥርዐት ገባ። ሰይጣን ወደ ሰይጣንነት የተቀየረበት የሞት ሥርዐትን ገባበት ማለት ነው” (ገጽ 11)። ከዚህ የዘላለም ጌታቸው አገላለጽ አኳያ ከታየ፣ “ኢየሱስ ሰየጠነ” ማለት ሰይጣን ወደ ሰይጣንነት የተቀየረበትን ሂደት ኢየሱስም ገባበት ማለት ነው፤ ወይም ኢየሱስም ወደ ሰይጣንነት ተቀየረ፤ ወይም የሰይጣንን ተፈጥሮ (ባሕርይ) ተካፈለ ማለት ነው።

 

         ስሕተት ወደ ስሕተት ይመራልና እነዚህ ሰዎች የኢየሱስን ወደ ሰይጣንነት መልለወጥ አስተምረው አያበቁም። ኢየሱስ ወደ ሲኦል ወርዶ በመንፈስ እንደ ሞተ እና እኛም የዳንነው በዚሁ ሂደት መሆኑን ጨምረው ያስተምራሉ። ለምሳሌ ኤልሻዳይ አበራ፣ ከላይ በተጠቀሰው መጽሐፉ፣ “ኢየሱስ የሥጋ ሞት ብቻ ሳይሆን በመንፈስም ሞቶ ነበር” ይልና “[ኢሳይያስ 53፥8] ‘ከሕያዋን ምድር እንደ ተወገደ’ ሲል በመንፈስ ሞቶ እንደ ነበር ወይም ከእግዚአብሔር መለየቱን ያስረዳል። አንዳንዶቻችን ሥራው በመስቀል ላይ ብቻ ያበቃ ይመስለናል። መጽሐፍ ቅዱስ ሲናገር ኢየሱስ ከሞተ በኋላ ወደ ሲኦል ወረደ ይላል። ኢየሱስ ወደ ሲኦል የወረደበት ምክንያት እኛን ከመንፈሳዊ ሞት ለማዳን መንፈሳዊ ሞት መሞት ስለ ነበረበት ነው” በማለት ያትታል (ገጽ 38)። በማስከተልም፣ “ክርስቶስ ወደ ሲኦል ወረደ፤ ለሰዎች የተሰጠውን የዘላለም ቅጣት ተቀጣ። ከእግዚአብሔር ተለየ” በማለት ጌታችን የዘላለም ቅጣት መቀበሉን ያስተምራል (ገጽ 39)።

 

በአሜሪካ የሚገኘው ኀይሉ ዮሐንስም ኢየሱስ ወደ ኀጢአትነት መቀየሩን ለማስተማር፣ ሰው የሰይጣንን ባሕርይ እንደ ተካፈለ ከመናገር ነው የሚጀምረው። በዩቲዩብ ድረ ገጽ ላይ በምናገኘው፣ “Hailu Yohannes @ Radison Blue Hotel 1” በሚለው ቪዲዮው እንደሚከተለው ሲያስተምር ይታያል። “ሰውን ኀጢአት ሲነካው፣ የሰይጣንን ባሕርይ ሲካፈል ሰው፣ የሰው መንፈስ ኀጢአት ሆነ። ኀጢአተኛ አይደለም የሆነው፤ የሰው መንፈስ ኀጢአት ሆነ። ለዚያ ነው ኢየሱስ ክርስቶስ፣ ‘ስለ እኛ ኀጢአት ሆነ’ የሚለው መጽሐፍ ቅዱስ። ሰው ኀጢአተኛ ቢሆን ኖሮ፣ ‘ኢየሱስ ክርስቶስ ኀጢአተኛ [ሆነ]’ ነበር  የሚባለው። ሰው እርግማን ነው የሆነው፤ ለዚያ ነው ኢየሱስ ከርስቶስ እርግማን መሆን ያስፈለገው።  [መጽሐፍ ቅዱስ] ‘ኢየሱስ የተረገመ ሆነ’ አይልም፤ ‘እርግማን ሆነ ነው’ የሚለው። Why? [ለምን? ሰው ኀጢአትን ሲያደርግ] የሰው መንፈስ እርግማን ነው የሆነው። የሰው መንፈስ ኀጢአት ስለሆነ ነው ኢየሱስ ኀጢአት የሆነው። … ኀጢአት በሠራ ጊዜ ሰው ኀጢአት ሆነ።” “Fear and Jesus” በሚለው ቪዲዮውም፣ “[ኢየሱስ] የአንድን ኀጢአተኛ ሰው ማንነት የወሰደበት ስፍራ ስለሆነ” በጌቴሴማኒ ፍርሀትና ድንጋጤ ታይቶበታል። ይኸውም፣ “ኀጢአት ሊሆን [ስለ ሆነ] ነው፤ መንፈሳዊ ሞት እየሞተ ነው ያለው፤ መስቀል ላይ ሲደርስ ሙሉ በሙሉ ከአብ ጋር ሊቆራረጥ ነው” በማለት ይጀምርና ኢየሱስ “ሙሉ በሙሉ ኀጢአት የሆነው መስቀል ላይ ሲደርስ ነው” በማለት ያሳርጋል።

 

ይህም ግን ለእነዚህ ሰዎች በቂ አይደለም። ስለዚህ ኢየሱስ በሲኦል ውስጥ ዳግመኛ መወለዱን ጨምረው ያስተምራሉ። በዱባይ የምትገኘው “የሕያው ክርስቶስ ዓለም አቀፍ ቤ/ክ” (Living Christ International Church) መጋቢ ፒተር ማርዲግ፣ ክርስቶስ አዲስ ፍጡር መሆኑን አስተምሯል። “ከመለኮት ጋር ያለ ሕይወት” በሚለው ስብከቱ፣ ኢየሱስ “እኔ አዲስ ፍጥረት ሆኜ ስነሣ [እናንተም] አዲስ ፍጥረት ሆናችሁ ትነሣላችሁ” በማለት መናገሩን አውስቷል። ይህ ሰው “የአንደበት ጉልበት” በሚለው ስብከቱም፣ ኢየሱስ ከ12 ዓመቱ ጀምሮ እስከ 30 ዓመቱ ድረስ በየመንደሩ እየዞረ “የእግዚአብሔር ልጅ ነኝ” በማለት “ኮንፌስ” ሲያደርግ በመኖሩ፣ በዕለተ ጥምቀቱ “ይህ የምወደው ልጄ ነው” በማለት ኮንፌሽኑን እግዚአብሔር እንዳረጋገጠለት ሲያስተምር ነበር፤ ስለዚህም ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅ የሆነው በኮንፌሽን ብዛት ነው ማለት ነው። ይህም ስብከቱ በኤልሻዳይ ቴሌቭዥን ኔትወርክ ተላልፏል፤ በዩቲዩብ ድረ-ገጽ ላይም ተጭኗል።

 

“4:12 Youth talk show” በተሰኘ፣ በኤልሻዳይ ቴሌቭዥን የሚተላለፍ ዝግጅት ቃለ ምልልስ ሲደረግለት፣ “ሬማ ባይብል ኮሌጅ” ትምህርቱን መከታተሉን የተናገረው ኤልሻዳይ አበራ ደግሞ፣ ኢየሱስ እንደ ማንኛውም አማኝ ዳግመኛ መወለዱን እና የዘላለም ሕይወት ማግኘቱን ነው የሚያስተምረው። ይህንንም ለማስረዳት “የመዋጀታችን እውነታዎች” የሚለው መጽሐፉ ቈላስይስ 1፥18ን፣ ዕብራውያን 1፥5-6ን እና ሮሜ 8፥29ን በመጥቀስ ይጀምራል። ከዚያም “መጀመሪያ ዳግመኛ በመወለድ የእግዚአብሔር ልጅ የሆነው ኢየሱስ ነው። ከሙታን በኵር የሚለው ቃል የሚያሳየው ከዘላለም ሞት ወደ ዘላለም ሕይወት ለመጀመሪያ ጊዜ የተሻገረው ክርስቶስ ኢየሱስ መሆኑን ነው። እግዚአብሔር ከሙታን ካስነሣው በኋላ ‘አንተ ልጄ ነህ ዛሬ ወልጄሃሁ’ አለው። ‘ዛሬ ወልጄሃለሁ’ ሲል፡- ኢየሱስ እኛን ለመዋጀት በእኛ ኀጢአት ምክንያት ልጅነቱን አጥቶ /የዘላለም ሞት ሞቶ እንደ ነበር/ ያስረዳል። ነገር ግን በትንሣኤው ኀይል ከሙታን በኩር ሆኖ በመነሣት ዳግመኛ ተወለደ” ሲል ያብራራል (ገጽ 46)። ስለዚህም፣ “ከዘላለም ሞት መጀመሪያ የተነሣ፣ የእግዚአብሔርን ልጅነት ዳግመኛ በመወለድ መጀመሪያ ያገኘ የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ነው። … ኢየሱስ በትንሣኤው ኀይል ከሙታን በኩር እና የመጀመሪያው የእግዚአብሔር ልጅ ሆኖ ተነሣ። ኢየሱስ ሲሞት ብቸኛ /አንድያ/ የእግዚአብሔር ልጅ ነበር” ሲል ተጨማሪ ማብራሪያውን ያክልበታል (ገጽ 47)።

 

ኀይሉ ዮሐንስም ጌታችን የእግዚአብሔር ልጅነቱን በመስቀል ላይ ማጣቱን ነው የሚያስተምረው። ጌታ ኢየሱስ “ሀብታም ሲሆን፣ እናንተ በእርሱ ድህነት ባለ ጠጎች ትሆኑ ዘንድ ስለ እናንተ ድሀ ሆነ” በማለት መጽሐፍ ቅዱስ የሚናገረውን ሐሳብ (2ቆሮ. 8፥9) “Prosperity II” በተሰኘ ስብከቱ ላይ በዚሁ መልኩ ነው የሚፈታው። በኀይሉ ዮሐንስ አገላለጽ፣ ጌታ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅ የሆነው ከድንግል ማርያም ሲወለድ ነው። ከዚያ በፊት የእግዚአብሔር ልጅ አልነበረም፤ ስለዚህም አብም፣ ወልድም መንፈስ ቅዱስም አባቶች ናቸው። እናም እግዚአብሔር ወልድ ሰው ሲሆን፣ ድሀ አልሆነም። ምክንያቱም የአባቱ የሆነው ሁሉ የእርሱ ነውና እግዚአብሔር ያለው ሁሉ እርሱም አለው።

 

ነገር ግን “ልክ ኢየሱስ ክርስቶስ በጌቴሴማኒ ሲደርስ … የእርሱን ብልጽግና እኛ እንድንወስድ፣ እርሱ ያለውን ነገር ማጣት ነበረበት። ያጣው ብርና ወርቅን አይደለም። ብርና ወርቅን include የሚያደርገውን [የሚያካትተውን] ልጅነቱን ነው ያጣው በመስቀል ላይ” ሲል ያስረዳል። ቀጥሎ ግን፣ ልጅነት ተፍቆ የሚጠፋ ነገር አለመሆኑን በመናገር ራሱን ይቃረናል። ከዚያም “በአብ ፊት በፍጹም አክሰሱ ተበጥሶ [ግንኙነቱ ተቋርጦ] ነበር።” ከዚህም የተነሣ፣ “ኢየሱስ ክርስቶስ የአባቴ የሆነው ሁሉ የእኔ ነው ማለት የሚችለው እስከ ጌቴሴማኒ ብቻ ነው። ከዚያ በኋላ የአባቱ የሆነው ሁሉ የእርሱ መሆኑ ቀረ” ሲል ሐሳቡን ያጠናክራል። የዚህም ምክንያቱ እግዚአብሔር ለእኛ  ያለው ፍቅር ሳይሆን፣ የሚያራምደው መርሕ ነው። “ኀጢአት የመጀመሪያው አዳም ላይም ሲታይ፣ ኋለኛው አዳም ላይም ሲታይ ያው ኀጢአት ነው!” “Fear and Jesus” በሚለው ቪዲዮውም እንደሚያትተው፣ “የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ መከራ እስከ መስቀል ብቻ አልነበረም። እስከ ሲኦልም ነበረ። ሦስቱን ቀናት ሙሉ በሙሉ ከአባቱ የተለየበትና ወደ ጨለማው ዓለም የወረደበት ነበር!”

 

  1. የጠማማው አስተምህሮ መሠረቶች

ከላይ የጠቀስናቸውም ሆኑ ስማቸው እዚህ ያልተጠቀሰ ሌሎች ሰዎች እነዚህን እና እነዚህን መሳይ ትምህርቶች ለማስተማር የሚመረኮዙባቸው አንዳንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶች አሉ። አንዳንዶቹ ጥቅሶቹን በግልጽ ያስቀምጣሉ፤ ጥቅሶቹን በግልጽ ሳያስቀምጡ ሐሳባቸውን ብቻ የሚያብራሩም አሉ። ዋናው ችግር ግን፣ በእነዚህ ሰዎች ዘንድ ዐውድ የሚባል ነገር ከቶም የማይታሰብ ጕዳይ መሆኑ ነው። እናም እነዚህን ጥቅሶች በየተራ እያነሣን ትክክለኛ ትርጓሜአቸውን ብንወያይ አግባብ ይሆናል።

 

2.1  ከሕያዋን ምድር መወገዱ (ኢሳይያስ 53፥8)

ነቢዩ ኢሳይያስ ስለ መሲሑ፣ “በማስጨነቅና በፍርድ ተወሰደ፤ ስለ ሕዝቤ ኀጢአት ተመትቶ ከሕያዋን ምድር እንደ ተወገደ ከትውልዱ ማን አስተዋለ?” በማለት መናገሩ ይታወቃል (53፥8)። ኤልሻዳይ አበራ በመጽሐፉ እንደሚናገረው ከሆነ፣ “‘ከሕያዋን ምድር እንደ ተወገደ’ ሲል በመንፈስ ሞቶ እንደ ነበር ወይም ከእግዚአብሔር መለየቱን ያስረዳል” (ገጽ 38)። ይህ ግን ተቀባይነት የሌለው ግምታዊ ትርጓሜ ነው። ምክንያቱም የሕያዋን ምድር ይህንን ምድራዊ ሕይወት፣ ይህንን ኑሮ የሚያሳይ በመሆኑ፣ ከሕያዋን ምድር መወገድ ማለት መሞት ማለት ነው።

 

ይህ ሐረግ ጥቅም ላይ የዋለባቸውን ሌሎች ስፍራዎች ከተመለከትን ሐሳቡ ግልጽ ይሆንልናል። አስቀድመን ይህንን ትንቢት ያስተላለፈውን የነቢዩ ኢሳይያስን አጠቃቀም ለመረዳት ከዚያው የኢሳይያስ መጽሐፍ መመልከት ይኖርብናል። ንጉሡ ሕዝቅያስ መሞቻው እንደ ደረሰ ሲነገረው፣ “በሕያዋን ምድር እግዚአብሔርን አላይም፣ በዓለምም ከሚኖሩ ጋር ሰውን እንግዲህ አልመለከትም” ብሎ እንደ ነበር ይናገራል (38፥11)። ይህም ሞትን የሚያሳይ አገላለጽ ነው። እግዚአብሔር ግን ጸሎቱን ሰምቶ ለምድራዊ ሕይወቱ ዕድሜ ጨመረለት።

 

ነቢዩ ኤርምያስም፣ “ዛፉን ከፍሬው ጋር እንቊረጥ፣ ስሙም ከእንግዲህ ወዲህ እንዳይታሰብ ከሕያዋን ምድር እናጥፋው” በማለት ተቃዋሚዎቹ ይዝቱበት እንደ ነበር እግዚአብሔር እስኪገልጥለት ድረስ ያውቅ እንዳልነበር ገልጿል፤ ስለዚህም እግዚአብሔር እንዲበቀልለት ልመናውን ያቀርባል (11፥18-20)። በዚህም ክፍል ውስጥ “ከሕያዋን ምድር እናጥፋው” ማለት እንግደለው ማለት እንጂ የመንፈስ ሞት እንዲሞት ወይም ከእግዚአብሔር ጋር ለዘላለም እንዲነጣጠል እናድርገው ማለት አይደለም።

 

ነቢዩ ሕዝቅኤል ደግሞ ስለ ጢሮስ በተነበየው ትንቢት ውስጥ፣ “ወደ ጕድጓድ ከሚወርዱት ጋር አወርድሻለሁ፤ የሚኖርብሽም እንዳይገኝ ወደ ጕድጓድ ከሚወርዱ ጋር ቀድሞ በፈረሰችው ስፍራ በታችኛዪቱ ምድር አኖርሻለሁ፤ ጌጥሽንም በሕያዋን ምድር አላኖርም። ለድንጋጤ አደርግሻለሁ፤ እንግዲህም አትኖሪም፤ ትፈለጊአለሽ፤ ለዘላለምም አትገኚም” የሚል ይገኝበታል (26፥19-21)። ይህም ሞትን፣ ውድመትን፣ ከዚህኛው ኑሮ ገለል መደረግን እንደሚያሳይ ግልጽ ነው። በተጨማሪም ሕዝቅኤል ምዕራፍ 32 ቊጥር 23ን፣ 24ን፣ 26ን እና 32ን መመልከት ይቻላል። ኢዮብም ሰዎች የጥበብን መገኛ ስፍራ አለማወቃቸውን ለመናገር፣ “ጥበብ የምትገኘው ወዴት ነው? የማስተዋልስ ስፍራ ወዴት ነው? ሰው መንገድዋን አያውቅም፤ በሕያዋን ምድር አትገኝም” ይላል (28፥13)። ይህ ምንባብ፣ ጥበብ በመንፈሳዊው ዓለም (በእግዚአብሔር ዘንድ) እንደማትገኝ አለማስተማሩ ግልጽ ነው። በመሆኑም “የሕያዋን ምድር” ማለት ይህኛው ዓለም፣ ይህኛው ኑሮ ማለት ነው!

 

ስለዚህ ኢሳይያስ መሲሑ ከሕያዋን ምድር እንደ ተወገደ ማየቱን ሲተነብይ፣ መሲሑ መገደሉን ወይም (ከዚህ ሕይወት በሞት ገለል መደረጉን) ለመናገር እንጂ፣ መሲሑ የመንፈስ ሞት መሞቱን ወይም ከእግዚአብሔር ጋር መለያየቱን ለመናገር አይደለም። የኢሳይያስ 53ን ዐውድ በቅጡ የሚያጤን አንባቢም እንዲህ አያስብም።

 

2.2  እርግማን መሆኑ (ገላትያ 3፥13)

ኤልሻዳይ አበራ እንደሚነግረን ከሆነ፣ “እርግማን ማለት … የሰይጣንን ሕይወት መካፈል ነው” (ገጽ 81)። “ከእርግማን በታች” መሆንም፣ “የሰይጣንን ደረጃ፣ የሰይጣንን ተፈጥሮ፣ የሰይጣንን ማንነት እና የሰይጣንን ሕይወት ተካፍሎ መኖር” ማለት ነው (ገጽ 15)። ስለዚህም ሐዋርያው ጳውሎስ “በእንጨት የሚሰቀል ሁሉ የተረገመ ነው ተብሎ ተጽፎአልና ክርስቶስ ስለ እኛ እርግማን ሆኖ ከሕግ እርግማን ዋጀን” በማለት ሲጽፍ (ገላ. 3፥13)፣ ክርስቶስ የሰይጣንን ሕይወት ተካፍሎ መኖሩን፣ የሰይጣንን ማንነት እና የሰይጣንን ደረጃ መውሰዱን ለመናገር መሆኑ ነው። ይህም ግን ከእውነት የራቀ አተረጓጐም ነው።

 

ሐዋርያው ጳውሎስ ቀደም አድርጎ እንደሚነግረን፣ “ሕግን በመጠበቅ የሚተማመኑ ሁሉ ከእርግማን በታች ናቸው” (ቊ. 10፤ አ.መ.ት)። ምክንያቱም ማንም ሕግን ሁሉ አሟልቶ መጠበቅ አይችልምና! ይህም እኛን ይመለከታል። ስለዚህም ክርስቶስ በእኛ ቦታ ገብቶ፣ በመስቀል ሥራው የእርግማን ሸክማችንን ከላያችን እንዳወረደው ነው ምንባቡ የሚናገረው።

 

ገላትያ 3፥10-13 “እርግማን” የሚለው፣ ይህንን በብሉይ ኪዳንን ሕግ ሥራ ጸንቶ አለመቆምን ነው፤ ክርስቶስ ሕግን ፈጽሞ በምትካችን በመስቀል ላይ ተሰቅሎ ይህንን እርግማን ስለ ሻረው፣ ማንም ሰው ወደ ክርስቶስ በሚመጣበት ጊዜ ነጻ ሆኖአል። አዲስ ኪዳን እንደሚያስተምረን በቀደመው አባታችን በአዳም ሁላችንም ተኮንነናል፤ በክርስቶስ ግን ጸጋው አጽድቆናል (ሮሜ 5፥15-21)። ስለዚህ ከክርስቶስ ውጭ ያለ ማንም ሰው ከእርግማን በታች ነው። ወደ ክርስቶስ ከመጣን በኋላ፣ በእርሱ ጽድቅ ሳይሆን በሕግ ሥራ ለመጽደቅ መጣር ኩነኔ ነው። የገላትያ ሰዎች በጸጋ ከዳኑበት መዳን የሐሰተኞችን ትምህርት ተቀብለው ፊታቸውን ወደ ሕግ ጥበቃ ማዞራቸው ነው ጳውሎስ ይህንን እንዲጽፍ ያደረገው።

 

ከዚህ በቀር፣ “እርግማን ማለት የሰይጣንን ሕይወት መካፈል” መሆኑን የሚያስረዳ አንድም የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጕም የለም፤ ኤልሻዳይ አበራም አንዳችም ማስረጃ አላስቀምጠም። እንዲሁ ብቻ የራሱን ብያኔ ነው ያስቀመጠው። በመሠረቱ አዳም ፍሬ በመብላቱ ለመጀመሪያ ጊዜ እርግማን ከወረደባቸው የፍጥረት አካላት መካከል መሬት ትገኝበታለች (ዘፍ. 3፥17)። ይህም ምድርን ከእርግማን በታች አድርጓታል። እናም “ከእርግማን በታች” መሆን፣ “የሰይጣንን ደረጃ፣ የሰይጣንን ተፈጥሮ፣ የሰይጣንን ማንነት እና የሰይጣንን ሕይወት ተካፍሎ መኖር” ማለት ከሆነ (ገጽ 15)፣ ምድርም የሰይጣንን ተፈጥሮ፣ የሰይጣንን ማንነት፣ የሰይጣንን ሕይወት ተካፍላ የምትኖር፣ የሰየጠነች ናት ማለት ነው?

 

2.3 ኀጢአት መደረጉ (2ኛ ቆሮንቶስ 5፥21)

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ፣ “እኛ በእርሱ [በክርስቶስ] ሆነን የእግዚአብሔር ጽድቅ እንሆን ዘንድ ኀጢአት ያላወቀውን እርሱን [ክርስቶስን] ስለ እኛ ኀጢአት አደረገው” ማለቱም በአንዳንድ የዘመኑ አስተማሪዎች በስሕተት የሚተረጐም ጥቅስ ነው (2ቆሮ. 5፥21)።

 

ሐዋርያው ጳውሎስ በዚህ ምንባብ እንደሚያስተምረው፣ ኢየሱስ ክርስቶስ ኀጢአትን ያላወቀ (ያላደረገ) ቢሆንም (ዕብ. 4፥15)፣ እንደ “ኀጢአት” እንዲቈጠር ተደረገ። አገላለጡ ልውውጥ ነው፤ አደራረጉም እኛ የእግዚአብሔር ጽድቅ በሆንንበት መንገድ እርሱ ስለ እኛ ኀጢአት የመሆኑ አደራረግ ነው። በብሉይ ኪዳን የመሥዋዕት ሕግ (ለምሳሌ ዘሌ. 1፥4፤ 16፥21፤ ወዘተ) ኀጢአተኛው በመሥዋዕቱ እንስሳ ላይ እጆቹን በመጫን ኀጢአቱን አስተላልፎ ራሱ ግን ይነጻል፤ የኀጢአተኛው ኀጢአት የተሸከመው በግም መሥዋዕት ይሆናል። ጌታችን ኀጢአታችንን ተሸክሞ በእኛ ቦታ በመግባት፣ ቅጣታችን የሆነውን የእግዚአብሔርን ቊጣ ተቀበለ። ለኀጢአተኛ የሚራራው፣ ነገር ግን በኀጢአት ላይ የሚጨክነው እግዚአብሔር አብም፣ “ኀጢአት በሆነው” በኢየሱስ ላይ ጨከነ። በዚህም እርሱ በእኛ ቦታ ገብቶ ከኀጢአት ስለ ተቈጠረልን፣ እኛ ከጽድቅ ተቈጠርን። የእኛን ኀጢአት እርሱ በመሸከሙ፣ እኛም የእርሱን ጽድቅ ተላበስን።

 

በመሠረቱ እኛ ከበሽታ ነጻ የወጣነው ክርስቶስ ሕመማችንን ተሸክሞ (የሕማም ሰው ሆኖ) ከሆነ፣ ከሞት ነጻ የወጣነው እርሱ ሞታችንን ተሸክሞ (ሞቶ) ከሆነ፣ ከእርግማን ነጻ የወጣነውም እርሱ እርግማናችንን ተሸክሞ (እርግማን ሆኖ)፣ ከኀጢአት ነጻ  የወጣነው እርሱ ኀጢአታችንን ተሸክሞ (ኀጢአት ሆኖ) ነው ማለት ነው።

 

ከዚህ በቀር ኢየሱስ ኀጢአትን ወይም ሰይጣንን ሆነ ሊባል አይቻልም።[14] ምክንያቱም በመጀመሪያ ደረጃ በዚህ ጥቅስ ውስጥ ኀጢአት የሚለው ቃል ጥቅም ላይ የዋለው በረቂቅ መልክ ነው። ቃሉ በቁሙ የሚወሰድ ባለመሆኑ፣ ክርስቶስም ሆነ ሌላ የትኛውም አካል ኀጢአት ሊሆን አይችልም።[15] ኀጢአት የሚለው ቃል ሌላን ሐሳብ (የኀጢአታችንን ቅጣት መሸከምን) ተክቶ የገባ አገላለጽ ነው።[16] “በዚህ ስፍራ ኀጢአት የሚለው ቃል የቀረበው በረቂቅ መልኩ በመሆኑ፣ ኢየሱስ ወደ ኀጢአትነት እንደ ተለወጠ ማስተማር፣ የኢየሱስን አዳኝነትና ሕላዌ (ማ         ንነት) ገፍፎ ወደ ረቂቅነት ማውረድ ነው።[17]

 

2.4 የሙታን በኵርነቱ (ቈላስይስ 1፥18)

“እርሱም [ክርስቶስ] በሁሉ ፊተኛ ይሆን ዘንድ መጀመሪያ፣ ከሙታንም በኵር ነው” (ቈላ. 1፥18)። ኤልሻዳይ አበራ ይህንን ጥቅስ ስለ ክርስቶስ የበኵር ልጅነት ከሚናገሩት ከዕብራውያን 1፥5-6 እና ከሮሜ 8፥29 ጋር አቀናጅቶ አላግባብ አቅርቦታል። ከዚያም ይህን ክፍል “ከዘላለም ሞት ወደ ዘላለም ሕይወት ለመጀመሪያ ጊዜ የተሻገረው ክርስቶስ ኢየሱስ መሆኑን” እንደሚናገር አድርጎ ያቀርብና፣ “ከዘላለም ሞት መጀመሪያ የተነሣ፣ የእግዚአብሔርን ልጅነት ዳግመኛ በመወለድ መጀመሪያ ያገኘ የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ነው” ሲል ይደመድማል (ገጽ 46-47)።

 

በመሠረቱ ከቈላስይስ በተጨማሪ የክርስቶስን የሙታን በኵርነት (የመጀመሪያነት) የሚናገሩ ሌሎች ጥቅሶችንም ማግኘት እንችላለን። ሐዋርያው ጳውሎስ፣ “አሁን ግን ክርስቶስ ላንቀላፉት በኵራት ሆኖ ከሙታን ተነሥቶአል” በማለት ጽፎአል (1ቆሮ. 15፥20)። “ክርስቶስ መከራን እንደሚቀበልና ከሙታን ቀዳሚ ሆኖ በመነሣት … ብርሃንን እንደሚሰብክ” ሙሴና ነቢያት መተንበያቸውን ሐዋርያው ጳውሎስ ሲሰብክ (የሐዋ. 26፥23፤ አ.መ.ት)፣ ሐዋርያው ዮሐንስ ደግሞ፣ “ከሙታንም በኵር የምድርም ነገሥታት ገዥ ከሆነ ከኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋና ሰላም ለእናንተ ይሁን” በማለት ለአብያተ ክርስቲያናት ሰላምታ ያቀርባል (ራእይ 1፥5)። ለመሆኑ፣ “የሙታን በኵር/ቀዳሚ/በኵራት/መጀመሪያ” ማለት ምን ማለት ነው?

 

ክርስቶስ የትንሣኤ በኵር/በኵራት/ቀዳሚ መሆኑ፣ የእኛን በትንሣኤ ተከታይነት ማሳወቁ እውነት ነው። ይህ ዐይነቱ ትንሣኤ ዳግመኛ መወለድን ነው የሚያመለክተው ወይስ በመጨረሻው ቀን የሚኖረውን ትንሣኤ? ለሚለው ጥያቄ ምላሽ ማግኘት ግን ከባድ ነገር አይደለም። የሙታን በኵርነቱ ዳግመኛ የመወለድ ሳይሆን፣ የሥጋ ትንሣኤን የማግኘት ነው።

 

ኢየሱስ ኀጢአተኛ አይደለምና ዳግመኛ መወለድ አያስፈልገውም። “ሰው ዳግመኛ ካልተወለደ በቀር የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊያይ አይችልም” የተባለው (ዮሐ. 3፥3) ለኀጢአተኛ ሰዎች ነው።[18] እርሱ ሁለተኛው ሞት ስለሌለበት ዳግም መወለድ አያስፈልገውም። ስለዚህም መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ኢየሱስ ውልደት ቢናገርም፣ ዳግም ውልደቱን በአንድም ስፍራ አይናገርም።

 

እርሱን አምነው የሞቱ እና የእርሱ የሆኑቱ እርሱ ዳግም ሲመጣ የእርሱን ዐይነት ትንሣኤ ያገኛሉ። በክብር ይነሣሉ። እርሱ በኵር የሆነው ለዚህ ዐይነቱ ትንሣኤ ነው። የሐዋርያው ጳውሎስ የቆሮንቶስ መልእክት ዐውድ ይህንን ግልጽ ያደርግልናል። “ነገር ግን ክርስቶስ ለሞቱት ከሞት የመነሣት በኵር ሆኖ በእርግጥ ከሞት ተነሥቷል። ሞት የመጣው በአንዱ ሰው በአዳም ምክንያት እንደ ሆነ ከሞት መነሣትም የሚመጣው በአንዱ ሰው በክርስቶስ ምክንያት ነው። በአዳም ምክንያት ሰው ሁሉ እንደሚሞት እንዲሁም በክርስቶስ ምክንያት ሰው ሁሉ ሕይወትን ያገኛል። ይህም የሚሆነው ለእያንዳንዱ በየተራው ነው፤ ክርስቶስ ከሞት የመነሣት የመጀመሪው ምሳሌ ነው፤ በኋላም ክርስቶስ በሚመጣበት ጊዜ የእርሱ የሆኑት ከሞት ይነሣሉ” (1ቆሮ. 15፥20-23፤ የ1997 ትርጕም)። ክርስቶስ የትንሣኤ በኵራት ነው፤ የእርሱን መሳይ ትንሣኤ የሚኖረው ደግሞ እርሱ ዳግመኛ ሲመጣ ነው።

 

ከክርስቶስ ትንሣኤ በፊት ከሞት የተነሡ ሰዎች በብሉይ ኪዳንም ሆነ (1ነገ. 17፥17-22፤ 2ነገ. 4፥32-35፤ 13፥21) በአዲስ ኪዳን (ሉቃ 7፥15፤ ዮሐ. 11፥44) መኖራቸውን ከመጽሐፍ ቅዱስ እናስተውላለን። ታዲያ እነዚህ ሁሉ ሰዎች በትንሣኤ ቀድመውት ሳለ፣ የክርስቶስ ትንሣኤ እንዴት የመጀመሪያ/ቀዳሚ/በኵራት/በኵር ሊሆን ይችላል? ብሎ መጠየቅ ተገቢ ጥያቄ ነው። እነዚህ ሁሉ ሰዎች በወቅቱ ከሞቱ ቢነሡም ተመልሰው ሞተዋል። የክርስቶስ ትንሣኤ ግን ከእነዚህ ሁሉ የተለየ ነው። ምክንያቱም፣ “ክርስቶስ ከሙታን ተነሥቶ ወደ ፊት እንዳይሞት ሞትም ወደፊት እንዳይገዛው እናውቃለንና” (ሮሜ 6፥9)!

 

ክርስቶስ ከሞት ሲነሣ የከበረ ሥጋ ለብሶ ነው የተነሣው፤ የትንሣኤው አካል (የከበረ ሥጋዊ አካል) የሚበሰብስ አይደለምና (1ቆሮ. 15፥42-43፤ 2ቆሮ. 5፥1)። ተመልሶ መምጣቱን የምንጠባበቀው ኢየሱስ፣ “ክቡር ሥጋውን እንዲመስል የተዋረደውን ሥጋችንን ይለውጣል” የተባለው ለዚህ ነው (ፊልጵ. 3፥20-21)። ጌታችን የዚህ ዐይነቱ ክቡር ትንሣኤ በኵር ነው። እርሱ በዚህ መልክ ከሙታን ተለይቶ በመነሣቱም እኛ የእግዚአብሔር ልጆች ሆነናል።

 

2.5 የተሰቀለው እባብ ምሳሌነት (ዮሐንስ 3፥14-15)

አንዳንዶች በግልጽ ባይናገሩትም፣ “ሙሴም በምድረ በዳ እባብን እንደ ሰቀለ እንዲሁ በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ የሰው ልጅ ይሰቀል [ዘንድ] ይገባዋል” የሚለውም የአስተምህሮአቸው መሠረት መሆኑ ይታወቃል (ዮሐ. 3፥14-15)። ኢየሱስ ካልሰየጠነ፣ እባቡ እንዴት የጌታ ኢየሱስ ስቅለት ምሳሌ ሊሆን ይችላል? ብለው ይጠይቃሉ።

 

ሰዎችን ለዚህ ዐይነቱ የተዛባ አተረጓጐም የሚዳርጋቸው ስለ ምሳሌ (ምልክት) ያላቸው መሠረታዊው ችግር ነው። ምልክቱ (ምሳሌው) የሚወከለውን ጕዳይ የሚወክለው ተለይቶ በተጠቀሰበት ጕዳይ ወይም ከተጠቀሰበት አቅጣጫ ብቻ እንጂ በነገር ሁሉ እንደሚወክለው ተደርጎ መታሰብ የለበትም። ለምሳሌ ጌታችን በሌላ ስፍራ የተናገረውን ተመሳሳይ ሐሳብ እንውሰድ። “ክፉና አመንዝራ ትውልድ ምልክት ይሻል፤ ከነቢዩም ከዮናስ ምልክት በቀር ምልክት አይሰጠውም። ዮናስ በዓሣ አንባሪ ሆድ ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት እንደ ነበረ፣ እንዲሁ የሰው ልጅ በምድር ልብ ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት ይኖራል” (ማቴ. 12፥39-40)። የዮናስ ምሳሌ የተነገረው ጌታችንም በመቃብር የሚቈይበትን ጊዜ ለማሳየት ብቻ ነው። ከዚያ ውጭ ሊወሰድ አይችልም። አሊያማ ዮናስ በዓሣ ነባሪው ሆድ ውስጥ የቈየው ሳይሞት ነውና ጌታችንም በመቃብር (በምድር ልብ) የሚቈየው ሳይሞት ነውን? በተጨማሪም ዮናስ በእግዚአብሔር ላይ ያመፀ ነቢይ ነውና ጌታችንም የሞተው በእግዚአብሔር ላይ ዐምፆ ነው ልንል ነው?

 

ጌታችን ስለ ሞቱ ዐይነት ለመናገር ሌሎች ምሳሌዎችንም ተናግሯል፤ እነዚህ ምሳሌዎች መወሰድ ያለባቸውም በዚሁ መልክ ነው። ለምሳሌ፣ “እኔም ከምድር ከፍ ከፍ ያልኩ እንደ ሆነ ሁሉን ወደ እኔ እስባለሁ። በምን ዐይነትም ሞት ይሞት ዘንድ እንዳለው ሲያመለክታቸው ይህን ተናገረ” የተባለው ለዚህ ነው (ዮሐ. 12፥32-33)። ስለዚህ፣ “ሙሴ በምድረ በዳ እባብን እንደ ሰቀለ፣ የሰው ልጅም እንዲሁ ሊሰቀል ይገባዋል” (ዮሐ. 3፥14-15፤ አ.መ.ት) ተብሎ የተነገረውም ከዚሁ በመነሣት ነው፤ በምን ዐይነት ሞት እንደሚሞት ለማመልከት!

 

የምድረ በዳው እባብ ታሪክ በዘኁልቁ 21 ተጽፎአል። ሙሴም ስለ ሕዝቡ ጸለየ። እግዚአብሔርም ሙሴን፦ እባብን ሠርተህ በዓላማ ላይ ስቀል የተነደፈውም ሁሉ ሲያያት በሕይወት ይኖራል አለው። ሙሴም የናሱን እባብ ሠርቶ በዓላማ ላይ ሰቀለ፤ እባብም የነደፈችው ሰው ሁሉ የናሱን እባብ ባየ ጊዜ ዳነ” (ቊ. 8-9)። እባቡ እንደ ተሰቀለ፣ ኢየሱስም ይሰቀላል፤ ማንነታቸው ግን ሊታሰብ ከሚችለው በላይ የተራራቀ ነው። የእነዚያ እና የእነዚህ (እኛንም ጨምሮ) መዳን የሚመሳሰለው እምነት በመኖሩ ነው። ይህንን ከዐውዱ በግልጽ መረዳት ይቻላል።  ከዚህ ውጭ ያለው ከክፉው ነው!

 

2.6 በኢየሱስ የሥጋ ሞት የመዳናችን ፍትሐዊነት

በዚህ ጽሑፍ ውስጥ ከተጠቀሱት የዚህ አስተምህሮ አራማጆች መካከል፣ ኢየሱስ በመንፈስ መሞቱን ወይም ዘላለማዊ ሞት መሞቱን የሚያስተምሩበትን ምክንያት ስጠይቅ አንደኛው አንድ ማብራሪያ ሰጥቶኛል። በዚህ ማብራሪያ መሠረት፣ ኢየሱስ የሥጋ ሞት ብቻ ሞቶ እኛን ከዘላለም ሞት ማዳኑ ተመጣጣኝ ክፍያ አይደለም። ስለዚህም ድነታችን ፍትሓዊ አይደለም፤ ወይም የተጭበረበረ ነው! የሥጋ ሞት ብቻ ከዘለዓለም ሞት ሊያድን ቢችል ኖሮ ማንም ፈቃደኛ የሆነ ሰው ሞቶ ያድነን ነበር። በመሆኑም ጌታችን በመስቀል ከሞተ በኋላ ቀሪውን የዘላለም ሞት ክፍያ ለማጠናቀቅ ወደ ሲዖል መውረድና በዚያ መንፈሳዊ (ዘላለማዊ) ሞት መሞት ያስፈልገዋል።

 

እዚህ ጋ ግን የፍትሓዊነት ነገር ከተነሣ አይቀር፣ አንዱ ስለ ሁሉ መሞቱ እና በአንዱ ሞት የዓለም ሁሉ ኀጢአት መወገዱ እንዴት ፍትሓዊ እንደሚሆን መጠየቅም ተገቢ ነው። የአንዱ ሥቃይ ለሰዎች ሁሉ የነጻነት መንገድ ማበጀቱ ፍትሐዊ ነውን? እንከን የለሹ ጌታ ያለ በደሉ መሞቱ፣ ከዚያም በደለኞቹ በእርሱ ሥቃይ መዳናቸውስ ከፍትሓዊነት አኳያ እንዴት ይታያል? የኢየሱስ የመስቀል ሞት ያስገኛቸው ትሩፋቶች በእግዚአብሔር ይሁንታ እና ዕቅድ ተገኝተው ሳለ፣ የፍትሓዊነት ጥያቄ መሰንዘር ምን ትርጕም ይሰጣል!? ቀድሞውኑስ ቢሆን፣ የፍትሕ ሚዛን፣ የፍትሕ መሠረት፣ የፍትሕ መነሻ እግዚአብሔር አይደለምን?

 

የዚህ ሁሉ ስሕተት መነሻው፣ የኢየሱስ ክርስቶስን ኀጢአት አልባ ማንነት ዋጋ አለመረዳት ነው። ኢየሱስ ቅዱስ ሕይወት ነበረውና የሥጋ ሞቱ ከመንፈስ ሞት ሊያድነን ይችላል! ጌታችን ኀጢአት አልነበረበትምና የእርሱ ሞት የሁላችንንም ኀጢአት ያስወግዳል! የናዝሬቱ ኢየሱስ ዘላለማዊ ሞት የሚሞት ሕይወት አልነበረውም፤ አስቀድሞም እርሱ የዘላለም ሕይወት ነበረው። መጽሐፍ እንደሚነግረን፣ “አብ በራሱ ሕይወት እንዳለው እንዲሁ ደግሞ አብ ለወልድ በራሱ ሕይወት እንዲኖረው ሰጥቶታል” (ዮሐ. 5፥26)። የዘላለም ሕይወት ሰጭም እርሱ ነው፤ “በእርሱ ሕይወት ነበረች፤ ሕይወትም የሰው ብርሃን ነበረች” (ዮሐ. 1፥4)። ታዲያ እንዴት የዘላለም ሞት ሊሞት ይችላል?

 

የትኛውም ሰው በሞቱ ሊያድነን ያልተቻለው፣ ሰው ሁሉ ኀጢአተኛ በመሆኑ ነው፤ ፈቃደኛ ሆኖ የመገኘት ጕዳይ አይደለም! ሰው ሁሉ ኀጢአተኛ በመሆኑ፣ ሰው ሁሉ አዳኝ ያስፈልገዋል፤ አዳኝ ለመሆን የበቃ ማንም የለም! ድነት ጽኑ እና አስተማማኝ መሠረትን ግድ ይላል። በአንድ ወቅት እስራኤላውያን ከእግዚአብሔር ቍጣ ይድኑና የተስፋዪቱን ምድር ይወርሱ ዘንድ ታላቁ ነቢይ ሙሴ ራሱን ለዘላለም ጥፋት በዕጩነት እስከ ማቅረብ ደርሶ ነበር (ዘጸ. 32፥30-32)፤ በሌላ ጊዜ ደግሞ ራሱ ሙሴ እግዚአብሔርን ባለመታዘዝ በደል በመፈጸሙ የተስፋዪቱን ምድር ከመውረስ ተከልክሏል (ዘኁ. 20፥7-12)። ሁልጊዜም እግዚአብሔርን የሚያስደስት፣ ሁልጊዜም ቅዱስና ጻድቅ ሕይወት ያለው፣ አንዳችም በደል የሌለበትና ለራሱ አዳኝ የማያስፈልገው ብቁ ማንነት የአዳኝነት መስፈርት ነው። አሊያ የዛሬው አዳኝ ነገ ኀጢአት እየሠራ፣ ድነታችን “ውሃ ቅዳ፣ ውሃ መልስ” በሆነ ነበር። በብሉይ ኪዳን በኀጢአት መሥዋዕትነት ይቀርቡ የነበሩት እንስሳት ነውር እና እንከን የሌለባቸው እንዲሆኑ የታዘዘው ከዚህ መነሻ ነበር (ዘሌ. 4፥3፡28፤ 9፥3፤ 6፥25-29፤ ዘዳ. 15፥21)። ኢየሱስም በኀጢአት የለሽነቱ ይህን አሟልቷል (ኢሳ. 53፥9፤ ሉቃ፣ 1፥35፤ ዮሐ. 8፥29፤ 19፥4፤ 2ቆሮ. 5፥21፤ ዕብ. 4፥15፤ 1ጴጥ. 1፥18-19፤ 2፥22)።

 

ሌላኛው የግንዛቤ ጉድለት ደግሞ የጌታ ኢየሱስ ልዩነትነት (uniqueness) አለማስተዋል ነው። በሰው እና በእግዚአብሔር መካከል እውነተኛ መካከለኛ የሚሆነው ከእግዚአብሔር ምንም የማያንስ ከእኛም በምንም ያልተለየ ባሕርይና አካል ያለው ማንነት ነው። ጌታችን ኢየሱስ በዚህ መልኩ በአንድ ጊዜ አምላክነትንም ሰውነትንም ወክሎ ሊገኝ ችሏል፤ እርሱ “ልክ እንደ እግዚአብሔር እግዚአብሔር ነው፤ ልክ እንደ እኛ ሰው ነው - ያለ ኀጢአት ከመሆኑ በስተቀር። … [እንደዚህ ዐይነት] ባሕርዮትና አካልነት ያለው ማንም የለም። ደግሞም ይህ ማንነት የማይደገምና የማይራባ ማንነት ነው።”[19] በመሆኑም ከኢየሱስ በቀር ሌላ አዳኝ የለም፤ ሊኖርም አይችልም!

 

የዓለምን ኀጢአት ሁሉ ዕዳ ለመሸከም፣ መለኮታዊ ፍቅር ያስፈልጋል። ኢየሱስ መለኮት በመሆኑ ይህ ፍቅር አለው! ራሱን ስለ ሌሎች ኀጢአት መሥዋዕት ለማድረግ ፈቃደኛ መሆን የሚመጣው እዚህ ጋ ነው። ከእግዚአብሔር በቀር፣ የትኛውም ሰው የዓለምን ኀጢአት ሁሉ ዕዳ ለመሸከም ዐቅምም አይኖረውም፤ ኢየሱስ እግዚአብሔር በመሆኑ የዓለምን የኀጢአት ሸክም ሁሉ ለመሸከም ይችላል። ሰው እግዚአብሔርን በድሏልና ሰውን ወክሎ በእግዚአብሔር ፊት ለመታየት የሚቻለው ብቁ (ኀጢአት የሌለበት) ሰው ያስፈልግ ነበር፤ ኢየሱስ ብቁ ሰው ነውና በእግዚአብሔር ፊት ሊወክለን ችሏል። ከኢየሱስ በቀር ይህ ልዩ ማንነት ያለው የለም! የኢየሱስ ልዩትነት ይህን ሁሉ ይሸፍናል!

  1. ወደ ኀጢአትነት እና ሰይጣንነት የተለወጠ ኢየሱስ?

ከላይ የተነሡትን ሐሳቦች ከሌሎች መጽሐፍ ቅዱሳዊና አመክንዮታዊ መርሖች አኳያ በማጤን ስሕተትነታቸውን መገንዘብም አይቸግርም።

 

ኢየሱስ የፍጹም ሰው የፍጹም አምላክ ባሕርያት የተገለጡበት አካል ነው። ታዲያ በጌቴሴማኒም ሆነ በመስቀሉ ላይ ወደ ሰይጣን ባሕርይ የተለወጠው የትኛው ማንነቱ ነው? ወደ ሰይጣን ባሕርይ የተለወጠው የሰውነት ባሕርይው ከሆነ፣ ኢየሱስ ፍጹም አምላክነት እና ፍጹም ሰይጣንነት የተጣመሩበት አካል (person) ሊሆን ነው። ይህ ደግሞ በጭራሽ ተቀባይነት የሌለው ነው። ሰይጣን እና እግዚአብሔር በአንድነት የተጣመሩበት አካል አዳኝም፣ አምላክም ሊሆን አይችልም። ኢየሱስ ሰይጣንነትን የተካፈለው አምላክነቱን አቁሞ ከነበረም፣ “ኢየሱስ ከመጀመሪያውም አምላክ አልነበረም ማለት ነው፤ እግዚአብሔርም ለቅጽበትም እንኳ አምላክ አለመሆን አይችልምና!”[20]

 

የሰየጠነው የኢየሱስ የመለኮትነት ባሕርይው ወይም መላው ማንነቱ ነው ከተባለ ደግሞ የሥላሴ አስተምህሮ ገደል ይገባል። ኢየሱስ እግዚአብሔር ወልድ በመሆኑ የሥላሴ ሁለተኛው አካል ነው። ስለዚህም እርሱ ከሰየጠነ ወይም ኀጢአት ወደ መሆን ከተለወጠ፣ አብ (አምላክ)፣ ወልድ (ማለትም ሰይጣን) እና መንፈስ ቅዱስ (አምላክ) በአንድነት አሐዱ አምላክ የሚሆኑበት ሥላሴ ሊኖር አይችልም። ይህ የሥላሴን ማንነት ያናጋል፤ ስለዚህም ይህ አስተምህሮ ሰይጣናዊ እንጂ መጽሐፍ ቅዱሳዊም ክርስቲያናዊም አይደለም። ይህንን የሚያምኑም ሥላሴያዊ አማኞች ሊሆኑ አይችሉም!

 

መጽሐፍ ቅዱሳዊው አስተምህሮ የሚነግረን የእግዚአብሔር ኑባሬአዊ ማንነት የማይነጣጠል መሆኑን ነው። እናም የእግዚአብሔር አካላት በዚህ መልክ ከተነጣጠሉ እና ከተከፋፈሉ የእግዚአብሔር ማንነታዊ ባሕርይ ይነጣጠልና ይጠፋል። መላለሙ ተደግፎ፣ ተጋጥሞ እና ጸንቶ የሚኖረው በእግዚአብሔር ነውና ከዚህ ክስተት የተነሣ መላለሙም መጥፋቱ አይቀርም።[21]

 

ክርስቶስ ወደ ኀጢአት፣ ወደ እርግማን እንደ ተለወጠና የሰይጣንን ተፈጥሮ ወደ መካፈል እንደ ደረሰ የሚናገሩ ሁሉ መጽሐፍ ቅዱሳዊውን የመሥዋዕት ሕግ በጭራሽ የሚያውቁ አይደሉም። የኀጢአት መሥዋዕት ሆኖ የሚቀርብ እንስሳ “ነውር የሌለበት” እንዲሆን ይጠበቃል (ዘሌ. 4፥3፡28፤ 9፥3)። እንስሳው ከታረደም በኋላ፣ “ቅዱሰ ቅዱሳን (እጅግ ቅዱስ)” በመሆኑ፣ ሥጋውን የሚነካ ሁሉ ይቀደሳል (ዘሌ. 6፥25-29)። ስለዚህም እስራኤላውያን፣ “ነውረኛ ወይም አንካሳ ወይም ዕውር ቢሆን፣ ወይም አንዳች ክፉ ነውር ቢኖረው ለአምላክህ ለእግዚአብሔር አትሠዋው” ተብለው ታዝዘዋል (ዘዳ. 15፥21)። ነውር እና እንከን ያለበት መሥዋዕት በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነት የለውም። ይህም የክርስቶስ ጥላ ነው።[22]

 

እንግዲህ ጌታ ኢየሱስም የፈጸመው ይህንኑ የብሉይ ኪዳን ትንቢት ነው። አዲስ ኪዳንም የሚነግረን ክርስቶስ፣ “መልካም መዐዛ ያለው መባና መሥዋዕት አድርጎ” ራሱን ለእግዚአብሔር እንዳቀረበ ነው (ኤፌ. 5፥2፤ አ.መ.ት)። በኀጢአት መሥዋዕትነት የታረደው እንስሳ ሥጋ እጅግ ቅዱስ እንደ ሆነ ሁሉ (ዘሌ. 6፥25-29)፣ ጌታችንም በመስቀል ላይ ሞቶ እንኳ ቅዱስነቱ እንደ ተጠበቀ ነበር።[23] ጌታችን በመስቀል ላይ “ነውር የሌለው ሆኖ በዘላለም መንፈስ ራሱን ለእግዚአብሔር” አቅርቧል (ዕብ. 9፥14)። ስለዚህም፣ “ነውርና እድፍ እንደሌለው እንደ በግ ደም በክቡር የክርስቶስ ደም እንደ ተዋጃችሁ ታውቃላችሁ” ተብለናል (1ጴጥ. 1፥18)። ታዲያ ወደ ሰይጣንነት የተለወጠ ኢየሱስ፣ ወደ ኀጢአትነት የተቀየረ ክርስቶስ በምን ታሪክ ነው “መልካም መዐዛ” ያለው መሥዋዕት አድርጎ ራሱን የሚያቀርበው? እንዴትስ ነው “ነውር የሌለው መሥዋዕት” የሚሆነው? ወይስ እነዚህ አስተማሪዎች፣ ሰይጣን ነውር የሌለበት ቅዱስ ባሕርይ አለው እያሉን ነው?

 

ኢየሱስ ከመስቀሉ በፊትም፣ በመስቀሉ ላይም ሆነ ከመስቀሉ በኋላ ወደ ሰይጣንነት፣ ወደ ኀጢአትነት አልተቀየረም። እርሱ የእኛን ኀጢአት ስለ መሸከሙ ነቢዩ ኢሳይያስ ሲናገር፣ “ጻድቅ ባሪያዬም … ኀጢአታቸውን ይሸከማል” በማለት ነው (53፥11)። ታዲያ የሰይጣንን ባሕርይ ተካፍሎ ሳለ፣ “ጻድቅ ባሪያዬ” በማለት እግዚአብሔር እንዴት ይጠራዋል? በመስቀል ላይ ሳለም፣ “አባት ሆይ፤ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው” ሲል ጸልዮአል (ሉቃ. 23፥34)። እናሳ እግዚአብሔር አብን “አባት ሆይ” ብሎ የሚጠራው ወደ ሰይጣንነት እና ወደ ኀጢአትነት የተለወጠው ኢየሱስ ነውን? ይህስ እግዚአብሔር አብን የኀጢአት ወይም የሰይጣን አባት አያደርገውን? መስቀል ላይ የዋለው የሰይጣንን ማንነት የተካፈለው (የሰየጠነው) ኢየሱስ ከሆነ፣ ከፍቅሩ የተነሣ ስለ ሕዝቡ ይቅርታ የሚለምነው ምን ዐይነት ሰይጣን ቢሆን ነው?[24]

 

ኢየሱስ ወደ ኀጢአትነት ከተለወጠ የአይሁድ ሸንጎ ለሞት አሳልፈው የሰጡት ኀጢአትን ነው ማለት ነው፤ ኀጢአት የሌለበትን አዳኝ አይደለም። ስለዚህ በፍርዳቸው ትክክል አድርገዋል ማለት ነው። እርሱ ግን አጠገቡ የተሰቀለውን ወንበዴ “ዛሬ በገነት ከእኔ ጋር ትሆናለህ” በማለት ነው መልሶላታል (ሉቃ. 23፥43)።[25] ታዲያ ሰይጣናዊ ባሕርይን የተካፈለ ወይም የሰየጠነ አካል መኖሪያው ገነት ሆነ ማለት ነው?

 

  1. የዳንነው በኢየሱስ የመስቀል ሞት? ወይስ በሲዖል ውስጥ እንግልቱ?

ድነት ያገኘነው በኢየሱስ የመስቀል ሞት ሳይሆን በሲኦል ውስጥ ሥቃዩ ነው በማለት ኤልሻዳይ አበራ እና መሰሎቹ ያስተምራሉ። ለምሳሌ “የመዋጀታችን እውነታዎች የሚለው መጽሐፍ፣ “አንዳንዶቻችን ሥራው በመስቀል ላይ ብቻ ያበቃ ይመስለናል። መጽሐፍ ቅዱስ ሲናገር ኢየሱስ ከሞተ በኋላ ወደ ሲኦል ወረደ ይላል። ኢየሱስ ወደ ሲኦል የወረደበት ምክንያት እኛን ከመንፈሳዊ ሞት ለማዳን መንፈሳዊ ሞት መሞት ስለ ነበረበት ነው” ሲል ያስተምራል (ገጽ 38)። በተጨማሪም “ክርስቶስ ወደ ሲኦል ወረደ፤ ለሰዎች የተሰጠውን የዘላለም ቅጣት ተቀጣ። ከእግዚአብሔር ተለየ፤ የዘላለምን ሞት ሞተ” ይላል (ገጽ 39)።

 

ይህ ዐይነቱ አስተምህሮ ከየትም ይምጣ ከየት መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ አያስተምርም። በመጀመሪያ ደረጃ፣ “ክርስቶስ ወደ ሲኦል ስለ መውረዱ ወይም ስላለመውረዱ፣ ከወረደ ደግሞ እንዴት እንደ ወረደና ምን ለማድረግ እንደ ወረደ መጽሐፍ ቅዱስ ግልጥ የሆነ ትምህርት አይሰጥም።”[26] ከዚህም የተነሣ ኢየሱስ በሞቱ ወደ ሲኦል መውረዱን ወይም ያለ መውረዱን የሚደግፉ የአስተሳሰብ ጎራዎች በየአብያተ ክርስቲያናት ሊኖሩ ይችላሉ።[27] ነገር ግን ኢየሱስ ወደ ሲኦል ወርዶ በሠራው ሥራ፣ ወይም በሲኦል ውስጥ በተፈጸመበት ነገር እንደ ዳንን ሊናገሩ አይችሉም፤ ይህ ጭልጥ ያለ ኑፋቄ ነውና! ምክንያቱም፣ “ክርስቶስ ለሰው ደኅንነት አስፈላጊውን መከራ ሁሉ የተቀበለው በጌቴሴማኒና በመስቀል ላይ ነበረ። … ወደ ሲኦል ከወረደም፣ የወረደው መከራን ለመቀበል አልነበረም።”[28] ድነትን ያህል ነገር መጽሐፍ ቅዱስ ላይ ባልተጻፈ ሁነት ላይ ሊመሠርቱ ከመጣር መጽሐፍ ቅዱስ የሚያስተምረውን አበክሮ መያዝ ሕይወት ይሆናል።

 

የዳንነው በክርስቶስ የመስቀል ጣር፣ የመስቀል ሞት፣ የመስቀል ሥራ ነው! ስለዚህም መጽሐፍ ቅዱስ በከፍተኛ ደረጃ በመስቀሉ ላይ ትኵረት ያደርጋል፤ መስቀሉ ወንጌልን የሚወክል ነውና! ለምሳሌ ሐዋርያው ጳውሎስ፣ “ወንጌሉ ከንቱ እንዳይሆን” ለማለት፣ “የክርስቶስ መስቀል ከንቱ እንዳይሆን” ይልና የወንጌሉን ቃልም “የመስቀሉ ቃል” ይለዋል (1ቆሮ. 1፥17 እና 18)። በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሳለም፣ “ከኢየሱስ ክርስቶስ በቀር እርሱም እንደ ተሰቀለ ሌላ ነገር እንዳላውቅ ቈርጬ ነበር” ብሎ ነበር (1ቆሮ. 2፥2)። የወንጌሉን ጠላቶችም፣ “ብዙዎች ለክርስቶስ መስቀል ጠላቶቹ ሆነው ይመላለሳሉ” ሲል ይገልጻቸዋል (ፊልጵ. 3፥18)። “ክርስቶስ በዐይናቸው ፊት እንደ ተሰቀለ ሆኖ ተሥሎ” ሲታያቸው የነበሩ አማኞችም፣ በዚያ ሁኔታ ባለመዝለቃቸው “አዚም ያደረገባችሁ ማን ነው?” በማለት ይጠይቃቸዋል (ገላ. 3፥1)። ትምክህቱንም ሲገልጽም፣ “ዓለም ለእኔ የተሰቀለበት እኔም ለዓለም የተሰቀልሁበት ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል በቀር ሌላ ትምክሕት ከእኔ ይራቅ” በሚል ፉከራ ነው (ገላ. 6፥14)። ስለዚህም የሐዋርያው ጳውሎስን ወንጌል የምንቀበል ከሆነ እኛም፣ “የተሰቀለውን ክርስቶስን እንሰብካለን” (1ቆሮ.1፥23)!

 

ሐዋርያው ጳውሎስ ብቻ ሳይሆን መላው መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ድነታችን ሲያወራ ስለ መስቀሉ ነው የሚያወራው። መላው መጽሐፍ ቅዱስ ድነታችንም ሆነ ከዚህ ጋር የተያያዙ በረከቶች ሁሉ የተገኙት በኢየሱስ ሞት፣ በደሙ እና በመስቀሉ መሆኑን ነው የሚመሰክረው። የኢየሱስ ደም የሚያሳየው የኢየሱስን ሞት ነው።[29] መስቀሉም የሚያሳየው ሥጋዊ ሞቱን ነው። ስለዚህ ደሙም፣ ሞቱም፣ መስቀሉም አንድን ነገር ነው የሚያመለክቱት ማለት ነው! ከዚህ ውጭ ኢየሱስ በሲኦል ውስጥ ተሠቃይቶ፣ በሲኦል ውስጥ በመንፈስ ሞቶ፣ በሲኦል ውስጥ ተወልዶ ድነትም ሆነ ጽድቅ ስለ ማግነታችን መጽሐፍ ቅዱስ አይናገርም።

 

አሁን ደግሞ በመስቀሉ፣ በሞቱ፣ በደሙ ያገኘናቸውን ከድነታችን ጋር የተገናኙ ክንውኖች ከመጽሐፍ ቅዱስ በዝርዝር እንመልከት።[30]

 

  • ከእግዚአብሔር ጋር የታረቅነው

“ጠላቶች ሳለን ከእግዚአብሔር ጋር በልጁ ሞት ከታረቅን …” (ሮሜ 5፥10)

“ጥልንም በመስቀሉ ገድሎ በእርሱ ሁለታቸውን በአንድ አካል ከእግዚአብሔር ጋራ ያስታርቅ ዘንድ ነው።” (ኤፌ. 2፥16)

“በእርሱም በኩል በመስቀሉ ደም ሰላም አድርጎ በምድር ወይም በሰማያት ያሉትን ሁሉ ለራሱ እንዲያስታርቅ ፈቅዶአልና።” (ቈላ. 1፥19-20)

“ልጁ በሥጋ በመሞቱ ምክንያት እግዚአብሔር ከራሱ ጋር አስታረቃችሁ።” (ቈላ. 1፥22፤ የ1997 ትርጕም)

 

  • የኀጢአት ስርየትና ይቅርታ የተገኘው

“ነፍሱን ስለ ኀጢአት መሥዋዕት ካደረገ በኋላ ዘሩን ያያል” (ኢሳ. 53፥10)

“ስለ ብዙዎች ለኀጢአት ይቅርታ የሚፈስ የአዲስ ኪዳን ደሜ ይህ ነው።” (ማቴ. 26፥28)

“እርሱንም [ኢየሱስ ክርስቶስንም] እግዚአብሔር በእምነት የሚገኝ በደሙም የሆነ ማስተስሪያ አድርጎ አቆመው” (ሮሜ 3፥25)

“መጽሐፍ እንደሚል ክርስቶስ ስለ ኀጢአታችን ሞተ …” (1ቆሮ. 15፥3)

“በውድ ልጁም እንደ ጸጋው ባለ ጠግነት መጠን በደሙ የተረገ ቤዛነታችንን አገኘን፤ እርሱም የበደላችን ስርየት።” (ኤፌ. 1፥7)

“ክርስቶስ ደግሞ፣ የብዙዎችን ኀጢአት ሊሸከም አንድ ጊዜ ከተሠዋ በኋላ …” (ዕብ. 9፥28)

“በዘላለም ኪዳን ደም ለበጎች ትልቅ እረኛ የሆነው ጌታችንን ኢየሱስን …” (ዕብ. 13፥20)

“ለወደደን ከኀጢአታችንም በደሙ ላጠበን …” (ራእይ 1፥6)

 

  • የእግዚአብሔር ፍቅርና ጸጋ የተገለጠው

“ገና ኀጢአተኞች ሳለን ክርስቶስ ስለ እኛ ሞቶአልና እግዚአብሔር ለእኛ ያለውን የራሱን ፍቅር ያስረዳል።” (ሮሜ 5፥8)

“ነፍሱን ስለ ወዳኞቹ ከመስጠት ይልቅ ከዚህ የሚበልጥ ፍቅር ለማንም የለውም።” (ዮሐ. 15፥13)

 

  • የጸደቅነው

“ይልቁንስ እንግዲህ አሁን በደሙ ከጸደቅን በእርሱ ከቊጣው እንድናለን።” (ሮሜ 5፥9)

ለኀጢአት ሞተን ለጽድቅ እንድንኖር፥ እርሱ ራሱ በሥጋው ኀጢአታችንን በዕንጨት ላይ ተሸከመ” (1ጴጥ. 2፥24)

 

  • ቤዛነታችንን ያገኘነው

“በውድ ልጁም እንደ ጸጋው ባለ ጠግነት መጠን በደሙ የተረገ ቤዛነታችንን አገኘን” (ኤፌ. 1፥7)

 

  • በእኛ ላይ ያለውን የሕግ ዕዳ የተሰረዘው

“ሲቃወመንና ሲጻረረን የነበረውን የዕዳ ጽሕፈት ከነሕግጋቱ በመደምሰሰ፣ በመስቀል ላይ ቸንክሮ ከመንገድ አስወገደው።” (ቈላ. 2፥14፤ አ.መ.ት)

 

  • ሰይጣናዊ ኀይላት የተሸነፉት

“የአለቆችንና የባለ ሥልጣናትንም ማዕረግ በመግፈፍ በመስቀሉ ድል ነሥቶ በአደባባይ እያዞራቸው እንዲታዩ አደረገ።” (ቈላ. 2፥15፤ አ.መ.ት)

“ይኸውም በሞት ላይ ኀይል ያለውን ዲያቢሎስን በሞቱ ኀይል እንዲደመስስ ነው” (ዕብ. 2፥14)

 

  • ታዛዥነቱ ጽድቃችን የሆነው

“ለሞትም፣ ይኸውም የመስቀል ሞት እንኳ የታዘዘ ሆነ።” (ፊልጵ. 2፥8)

 

  • ከሕግ እርግማን የተዋጀነው

“በእንጨት የሚሰቀል ሁሉ የተረገመ ነው ተብሎ ተጽፎአልና ክርስቶስ ስለ እኛ እርግማን ሆኖ ከሕግ እርግማን ዋጀን” (ገላ. 3፥13)

 

  • ለጽድቅ መሠረት የሆኑትን ግርዛትና መሰል ሃይማኖታዊ ሥርዐቶች የተሻሩት

“ወንድሞቼ ሆይ! እኔ እስካሁን የምሰብከው፣ ለመዳን መገረዝ ያስፈልጋል እያልኩ ቢሆን ኖሮ እስከ አሁን ለምን ያሳድዱኝ ነበር? እንዲህ ቢሆን ኖሮ የክርስቶስ መስቀል ለሰዎች እንቅፋት መሆኑ ይቀር ነበር።” (ገላ. 5፥11፤ የ1997 ትርጕም)

 

  • ውስ ያገኘነው

“ስለ መተላለፋችን ቈሰለ፤ ስለ በደላችንም ደቀቀ … በእርሱ ቊስል እኛ ተፈወስን።” (ኢሳ. 53፥5)

 

  • ንጹሕ ኅሊና ሊሰጠን

“ነውር የሌለው ሆኖ በዘላለም መንፈስ ራሱን ለእግዚአብሔር ያቀረበ የክርስቶስ ደም እንዴት ይልቅ ሕያውን እግዚአብሔርን ልታመልኩ ከሞተ ሥራ ሕሊናችሁን ያነጻ ይሆን?” (ዕብ. 9፥14)

 

  • የእግዚአብሔር እንድንሆን

“በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ..” (የሐዋ. 20፥28)

 

  • ቅዱሳንና ፍጹማን ሊያደርገን

“ፋሲካችን ክርስቶስ ታርዶአልና ስለዚህ በቅንነትና በእውነት ቂጣ በዓልን እናድርግ እንጂ በአሮጌ እርሾ በክፋትና በግፍ እርሾም አይደለም” (1ቆሮ. 5፥7-8)

“እናንተንም ነውርና ነቀፋ የሌላችሁና ቅዱሳን አድርጎ በእርሱ ፊት ያቀርባችሁ ዘንድ፣ በፊት የተለያችሁትን ክፉ ሥራችሁንም በማድረግ በአሳባችሁ ጠላቶች የነበራችሁትን አሁን በሥጋው ሰውነት በሞቱ በኩል አስታረቃችሁ።” (ቈላ. 1፥21-22)

“ስለዚህ፥ ኢየሱስ ደግሞ በገዛ ደሙ ሕዝቡን እንዲቀድስ ከበር ውጭ መከራን ተቀበለ።” (ዕብ. 13፥12)

 

  • ወደ እግዚአብሔር የቀረብነው

“አሁን ግን እናንተ በፊት ርቃችሁ የነበራችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ ሆናችሁ በክርስቶስ ደም ቀርባችኋል።” (ኤፌ. 2፥13)

“ክርስቶስ ደግሞ ወደ እግዚአብሔር እንዲያቀርበን እርሱ ጻድቅ ሆኖ ስለ ዓመፀኞች አንድ ጊዜ በኀጢአት ምክንያት ሞቶአልና” (1ጴጥ. 3፥18)

 

  • ወደ ቅድስተ ቅዱሳን መግባት ድፍረት እንድናገኝ

“በመረቀልን በአዲስና ሕያው መንገድ ወደ ቅድስት በኢየሱስ ደም በመጋረጃው ማለት በሥጋው በኩል እንድንገባ ድፍረት ስላለን …” (ዕብ. 10፥19)

 

  • ከወረስነው ከንቱነት ሊታደገን

“ነውርና እድፍ እንደ ሌለው እንደ በግ ደም በክቡር የክርስቶስ ደም እንደ ተዋጃችሁ ታውቃላችሁ።” (1ጴጥ. 1፥18-19)

 

  • ለክርስቶስ እንጂ ለራሳችን እንዳንኖር

በሕይወትም ያሉት ስለ እነርሱ ለሞተውና ለተነሣው እንጂ ወደ ፊት ለራሳቸው እንዳይኖሩ ስለ ሁሉ ሞተ።” (2ቆሮ. 5፥15)

 

  • መስቀሉን የትምክህታችን ሁሉ መሠረት ለማድረግ

“ነገር ግን፥ ዓለም ለእኔ የተሰቀለበት እኔም ለዓለም የተሰቀልሁበት ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል በቀር ሌላ ትምክሕት ከእኔ ይራቅ።” (ገላ. 6፥14)

 

  • ምሳሌውን እንድንከተል

“በክርስቶስ ኢየሱስ የነበረ ይህ አሳብ በእናንተ ዘንድ ደግሞ ይሁን። እርሱ በእግዚአብሔር መልክ ሲኖር ሳለ ከእግዚአብሔር ጋራ መተካከልን መቀማት እንደሚገባ ነገር አልቈጠረውም፥ ነገር ግን፥ የባሪያን መልክ ይዞ በሰውም ምሳሌ ሆኖ ራሱን ባዶ አደረገ፥ በምስሉም እንደ ሰው ተገኝቶ ራሱን አዋረደ፥ ለሞትም ይኸውም የመስቀል ሞት እንኳ የታዘዘ ሆነ።” (ፊልጵ. 2፥5-8)

“የእምነታችንንም ራስና ፈጻሚውን ኢየሱስን ተመልክተን፣ በፊታችን ያለውን ሩጫ በትዕግሥት እንሩጥ፤ እርሱ ነውርን ንቆ በፊቱም ስለ አለው ደስታ በመስቀል ታግሦ በእግዚአብሔር ዙፋን ቀኝ ተቀምጦአልና።” (ዕብ. 12፥2)

 

  • የተበተኑትን በጎቹን ለመሰብሰብ

ሕዝቡም ሁሉ ከሚጠፋ አንድ ሰው ስለ ሕዝቡ ይሞት ዘንድ እንዲሻለን አታስቡም አላቸው። … ስለ ሕዝቡም ሁሉ አይደለም፥ ነገር ግን፥ የተበተኑትን የእግዚአብሔርን ልጆች ደግሞ በአንድነት እንዲሰበስባቸው ነው እንጂ።” (ዮሐ. 11፥50-52)

 

  • በዘሮች መካከል ያለውን ጠላትነት ለማስወገድ

“እርሱ ሰላማችን ነውና፤ ሁለቱን ያዋሐደ በዐዋጅ የተነገሩትንም የትእዛዛትን ሕግ ሽሮ በመካከል ያለውን የጥል ግድግዳን በሥጋው ያፈረሰ፤ ይህም ከሁለታቸው አንድን ዐዲስን ሰው በራሱ ይፈጥር ዘንድ ሰላምንም ያደርግ ዘንድ፥ ጥልንም በመስቀሉ ገድሎ በእርሱ ሁለታቸውን ባንድ አካል ከእግዚአብሔር ጋራ ያስታርቅ ዘንድ ነው።” (ኤፌ. 2፥14-16)

 

  • ሕዝቦችን ከነገድ፣ ከቋንቋ ሊዋጅ

“ታርደሃልና፥ በደምህም ለእግዚአብሔር ከነገድ ሁሉ ከቋንቋም ሁሉ ከወገንም ሁሉ ከሕዝብም ሁሉ ሰዎችን ዋጅተህ፣ ለአምላካችን መንግሥትና ካህናት ይሆኑ ዘንድ አደረግሃቸው” (ራእይ 5፥9)

 

  • ከሞት በኋላ ወዲያውኑ ከእርሱ ጋር እንድንሆን

የምንነቃም ብንሆን፥ የምናንቀላፋም ብንሆን፥ ከእርሱ ጋራ ዐብረን በሕይወት እንኖር ዘንድ ስለ እኛ ሞተ።” (1ተሰ. 5፥10)

 

  • በወንጌሉ ውስጥ የእግዚአብሔርን ኀይል ለመግለጥ

“የመስቀሉ ቃል ለሚጠፉት ሞኝነት፥ ለእኛ ለምንድን ግን የእግዚአብሔር ኀይል ነውና።” (1ቆሮ. 1፥18)

 

  • የብሉይ ኪዳኑን ክህነት በማስቆም ዘላለማዊ ሊቀ ካህናት ሊሆን

“እርሱም እንደነዚያ ሊቃነ ካህናት አስቀድሞ ስለ ራሱ ኀጢአት በኋላም ስለ ሕዝቡ ኀጢአት ዕለት ዕለት መሥዋዕትን ሊያቀርብ አያስፈልገውም፤ ራሱን ባቀረበ ጊዜ ይህን አንድ ጊዜ ፈጽሞ አድርጓልና።” (ዕብ. 7፥27)

ሊቀ ካህናትም በየዓመቱ የሌላውን ደም ይዞ ወደ ቅድስት እንደሚገባ፥ ራሱን ብዙ ጊዜ ሊያቀርብ አልገባም፤ እንዲህ ቢሆንስ፥ ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ ብዙ ጊዜ መከራ ሊቀበል ባስፈለገው ነበር፤ አሁን ግን በዓለም ፍጻሜ ራሱን በመሠዋት ኀጢአትን ሊሽር አንድ ጊዜ ተገልጧል።” (ዕብ. 9፥25-26)

 

  • ለክብሩ

“በእግዚአብሔር ጸጋ ስለ ሰው ሁሉ ሞትን ይቀምስ ዘንድ፥ ከመላእክት ይልቅ በጥቂት አንሶ የነበረውን ኢየሱስን ከሞት መከራ የተነሣ የክብርና የምስጋናን ዘውድ ተጭኖ እናየዋለን።” (ዕብ. 2፥9)

“በታላቅም ድምፅ፦ የታረደው በግ ኀይልና ባለጠግነት ጥበብም ብርታትም ክብርም ምስጋናም በረከትም ሊቀበል ይገባዋል አሉ።” (ራእይ 5፥12)  

 

4.1 መስቀል ዓርማችን ወይስ ሲኦል ዓርማችን?

እነዚህና እነዚህን የመሳሰሉ የመጽሐፍ ቅዱስ ምንባባት የሚያስተምሩን መስቀሉ የሁሉ ነገር ማዕከል መሆኑን ነው። የዳንነው፣ ከእግዚአብሔር ጋር  የታረቅነው፣ የጸደቅነው፣ ሰይጣን የተሸነፈው፣ ኀጢአታችን የተሰረየው፣ ከዘላለም ፍርድ የተረፍነው፣ … ሁሉም የሆነው በመስቀሉ፣ በሞቱ፣ በደሙ ነው። ከዚያ ውጭ ክርስቶስ ወደ ሲኦል ወርዶ በደረሰበት እና ባደገረው ነገር መዳናችንንም ሆነ አንዳች ማግኘታችንን መጽሐፍ ቅዱስ አያስተምርም!

 

ሐዋርያው ጴጥሮስ በመጀመሪያ መልእክቱ እንደሚያስተምረው፣ ጌታ ኢየሱስ “በሥጋው ኀጢአታችንን ተሸከመ” (2፥24)፤ “በሥጋ ስለ እኛ መከራ ተቀበለ” (4፥1)፤ “በሥጋ ሞተ” (3፥18)። የዳንነው በሥጋ ሞቱ እንጂ በመንፈስ ሞቱ አይደለም። የዳንነው ጌታ ኢየሱስ በመስቀል ተሰቅሎ፣ ደሙን አፍስሶ፣ በሥጋ በመሞቱ ነው። ጌታችን በሲኦል ውስጥ በመንፈስ ሞቶ፣ ወይም በሲኦል ውስጥ ልጅነቱን አጥቶ አይደለም ያጸደቀን። ኢየሱስ ከአባቱ ጋር አልተለያየም። ጌታችን በመስቀል ላይ ኀጢአታችንን ተሸክሞ አካላዊ እና ስሜታዊ ሥቃይን ተቀብሏል። በእኛ ላይ የነበረው የእግዚአብሔር ቊጣ ተሰምቶታል። ከዚያ ውጭ ግን ከእግዚአብሔር ጋር ተለያይቷል ማለት አንችልም፤ እግዚአብሔር ከእግዚአብሔር ጋር ሊለያይ አይችልምና። ምክንያቱም ኢየሱስ በሥጋ የተገለጠ እግዚአብሔር ነውና እግዚአብሔር ነው። በሰዋዊ ማንነቱ ከእግዚአብሔር ጋር የመለያየት ስሜት ቢኖረው እንኳ፣ በእግዚአብሔር ወልድነቱ ከእግዚአብሔር አብ ጋር ሊለያይ አይችልም ነበር![31]

 

ኢየሱስ፣ “አምላኬ አምላኬ፣ ስለ ምን ተውከኝ?” ብሎ መጸለዩን ከእግዚአብሔር ጋር እንደ መለያየት ተደርጎ ቢወሰድ እንኳ (ማቴ. 27፥46)፣ ይህን ያለው በመስቀል ላይ እንጂ በሲኦል እንዳልሆነ መታወቅ አለበት። ሲሞትም፣ “አባት ሆይ፤ ነፍሴን በእጅህ አደራ እሰጣለሁ” (ሉቃ. 23፥46) በማለት መሆኑ ከእግዚአብሔር ጋር የነበረው መለያየት እዚያው በመስቀል ላይ የማብቃቱ ማረጋገጫ መሆን ይችላል! ከዚህ አስቀድሞም፣ አጠገቡ ለተሰቀለውና ንስሓ ለገባው ሰው፣ “እውነት እልሃለሁ፤ ዛሬ ከእኔ ጋር በገነት ትሆናለህ” ማለቱም ለዚህ ጕዳይ ቊልፍ ነው (ሉቃ. 23፥43)። ይህም ጌታችን በሥጋ እንደ ሞተ ወዲያውኑ ከሥቃዩ ተላቅቆ በአባቱ እቅፍ ማረፉን የማሳየት አንድምታ አለው። ጌታ ኢየሱስ በሞቱና በትንሣኤው መካከል ለመንፈሳዊ  ሞት ተዳርጎ፣ ከአብ ጋር ተለያይቶ እንደ ቈየ የሚያትተውንም አስተምህሮ ይቃረናል።[32]

 

ከዚህ የተለየ ሐሳብ ለማስተናገድ መጽሐፍ ቅዱስ ዕድል አይሰጥም። ምክንያቱም ጌታችን በመስቀል ላይ “ተፈጸመ” ሲል የተናገረው፣ የድነት ሥራ በመስቀል ላይ ስለ ተፈጸመ ነው (ዮሐ. 19፥30)። ትንሣኤው ያ “ተፈጸመ” የተባለው ጕዳይ የመፈጸሙና መሥዋዕቱ ተቀባይነት የማግኘቱ ምስክር ነው እንጂ፣ የተፈጸመው ነገር በትክክልም የተፈጸመው ግን በመስቀሉ ላይ ነው። እናም የዳንነው ኢየሱስ ሲዖል ወርዶ በፈጸማቸው ወይም በተፈጸሙበት ድርጊቶች ነው ብሎ ማመን፣ እርሱ በመስቀል ላይ ሆኖ “ተፈጸመ” ያለውን “አልተፈጸመም” በሚል ማስተካከል ይሆናል። ይህም በቅዱስ ቃሉ ላይ ማመፅ ነው። የእግዚአብሔር ልጅ በእርግጥም “ተፈጸመ” ያለውን ነገር “አልተፈጸመም” ብሎ ማስተማር፣ የከፋ ስሕተትና በዚያ የከበረ መሥዋዕት ላይ ጢቅ እንደ ማለት ነው። ዕብሪት ነው!

 

በመሠረቱ ሕዝበ ክርስቲያኑ መስቀሉን በየቤተ ክርስቲያኑ ጉልላት ላይ የሚተክለው እና በየቤቱ የሚሰቅለው፣ በዐንገቱ የሚያጠልቀው እና በገላው ላይ የሚነቀሰው፣ በአጠቃላይም መስቀሉ የክርስትና መገለጫ የሆነው በመስቀል ሥራ ስለ ዳንን ነው። መስቀሉ ዓርማችን፣ መስቀሉ ሰንደቅ ዓላማችን የሆነው በመስቀል ጣር ስለ ተወለድን ነው። መስቀሉ በመስቀል የሞተልን ጌታ መታሰቢያ ሆኖልናል። የዳንኩት በመስቀል ላይ ሥራው ሳይሆን በሲዖል ውስጥ ሥራው ነው የሚል ሰው፣ መስቀሉን አውርዶ የሲኦልን ዓርማ አንግቦ ወይም አንጠልጥሎ መዞር ይችላል!

 

የግርጌ ማስታወሻ

[1] Blaise Pascal, Pansées 29. ፈረንሳዊው የሒሳብ እና የፊዚክስ ሊቅ ብሌይስ ፓስካል (1623-1662)፣ L’Apologie de la religion chrétienne የሚል ርእስ ያለው ክርስቲያናዊ የዕቅበተ እምነት መጽሐፍ ማሳተም ቢፈልግም፣ ዓላማውን ከግብ ሳያደርስ በ39 ዓመቱ ተቀጭቷል። ለዚህ መጽሐፍ ያዘጋጃቸው ማስታወሻዎች ግን ከፓስካል ሞት በኋላ ተሰብስበውና ቊጥር ተሰጥቷቸው በሉዊስ ላፉማ (Louis Lafuma) አዘጋጅነት Pensées በሚል ርእስ ታትመዋል። William Lane Craig, Reasonable Faith: Christian Truth and Apologetics, 3rd ed. (Wheaton: Crossway, 2008), 66.

[2] Robert M. Bowman Jr., The Word-Faith Controversy: Understanding the Health and Wealth Gospel, unabridged edition (by the author, 2013), 164.

[3] Leon Morris, The Cross in the New Testament (Carlisle: Paternoster, 1965), 365.

[4] Hank Hanegraaff, Christianity in Crisis: 21st Century (Nashville: Thomas Nelson, 2009), 190.

[5] John R. W. Stott, The Cross of Christ (Downers Grove: IVP, 2006), 71.

[6] ምኒልክ አስፋው፤ “ኢየሱስ ክርስቶስ ትናንት፣ ዛሬና ነገ” ተስፋ መጽሔት፣ ቅጽ 1 ቊጥር 1 Mar-May, 2014 ገጽ 6።

[7] J. I. Packer, Knowing God (London: Hodden & Stoughton, 1973), 314.

[8] እነዚህ ሰዎች እዚህ የተጠቀሱትን ሐሳቦች ጨምሮ በሁሉም ነገረ ክርስቶሳዊ አስተምህሮዎች ተመሳሳይ አቋም ላይኖራቸው ይችላል። ለምሳሌ ዘላለም ጌታቸው፣ ጌታ ኢየሱስ ከድንግል ማርያም ከመወለዱም በፊት የእግዚአብሔር ልጅ ስለ መሆኑ ያስተምራል (“የሰው አፈጣጠርና ውድቀት” የሚል ስብከቱን ይመለከቷል!)። ኀይሉ ዮሐንስ ግን ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅ የሆነው ከድንግል ማርያም ሲወለድ እንጂ ከዚያ በፊት አባት እንጂ ልጅ እንዳልነበር የሚገልጽ የተሳከረ ትምህርት አለው (ለምሳሌ፣ “The Concept of Trinity” የሚለውን ስብከቱን ይመለከቷል!)።

[9] ወደ ኢትዮጵያ መጥታ ወንጌላውያን አብያተ ክርስቲያናትን ለማገልገል ዕድል ያገኘችው ጆይስ ሜየር እና በቅርቡ እንደሚመጣ የተነገረለት ቤኒ ሂንን ጨምሮ፣ ኬኒት ሄገን፣ ኬኒት ኮፕላንድ፣ ፍሬድሪክ ፕራይስ፣ ክሬፍሎ ዶላር እና እነርሱን የሚከተሉ ሌሎች ግለ ሰቦች፣ ክርስቶስን የሚያራክሱ እና መስቀሉን ዋጋ የሚያሳጡ የእነዚህ ትምህርቶች አቀንቃኞች መሆናቸው ይታወቃል። (Hanegraaff, Christianity in Crisis, 171-190.) በዚህ ጽሑፍ በስም የተጠቀሱ ኢትዮጵያውን የሚያሰራጯቸው እነዚህ ኢ-መጽሐፍ ቅዱሳዊ ትምህርቶችም ከእነዚህ አሜሪካውያን የተቀዱ ናቸው።

[10] ዘላለም መንግሥቱ እና አማረ መስፍን ይህን ጽሑፍ አስቀድመው በማንበብ ጠቃሚ አስተያየቶችን አድርገዋል።

[11] ኤልሻዳይ አበራ፤ የመዋጀታችን እውነታዎች (ጆሀንስበርግ፡ 2014)

[12] ከዚህ በኋላ ይህ መጽሐፍ ሲጠቀስ፣ የግርጌ ማስታወሻውን ላለማብዛት ሲባል የገጽ ቊጥሮቹ እዚያው እንዲመላከቱ ተደርጓል።

[13]ማራናታ መጽሔት፤ ቊጥር 4 ሰኔ/ሐምሌ 2008 እትም፤ አዲስ አበባ።

[14] ስለዚህም አዲሱ መደበኛ ትርጕም ወይም የእንግሊዝኛው NIV “ኀጢአት አደረገው” ለሚለው አገላለጽ “የኀጢአት መሥዋዕት አደረገው” ወይም “be a sin offering” የሚለውን በአማራጭ ትርጕምነት በግርጌ ማስታወሻቸው አመልክተዋል።

[15] Thomas J. Crawford, The Doctrine of Holy Scripture Respecting the Atonment (Grand Rapids: Baker Books, 1954), v. ከHanegraaff, Christianity in Crisis, 174 የተወሰደ።

[16] Braian Onken, “The Atonment of Christ and the ‘Faith’ Messge,” Forwared 7, 1 (1984): 11-12. ከHanegraaff, Christianity in Crisis, 174 የተወሰደ።

[17] Hanegraaff, Christianity in Crisis, 174.

[18] ዝኒ ከማሁ፤ ገጽ 183።

[19] ምኒልክ አስፋው፤ “ኢየሱስ ክርስቶስ ትናንት፣ ዛሬና ነገ” ተስፋ መጽሔት፣ ቅጽ 1 ቊጥር 1 Mar-May, 2014 ገጽ 11።

[20] Bowman Jr.,Word-Faith Controversy, 170.

[21] Hanegraaff, Christianity in Crisis, 172.

[22] ዝኒ ከማሁ፤ ገጽ 174።

[23] ዝኒ ከማሁ።

[24] ዝኒ ከማሁ፤ ገጽ 175-76።

[25] ዝኒ ከማሁ፤ ገጽ 173።

[26] ኮሊን ማንስል፤ ትምህርተ ክርስቶስ፡ አጠቃላይ የነገረ መለኮት ትምህርት፤ 2ኛ መጽሐፍ (አዲስ አበባ፤ 1999) ገጽ 201።

[27] ኢየሱስ ወደ ሲኦል እንዳልወረደ የሚያስረዱ ጽሑፎችን ማግኘት ይቻላል። ጳውሎስ ፈቃዱ፤ ኢየሱስ በሞቱ ወደ ሲኦል ወርዶአልን? (አዲስ አበባ፤ ግንቦት 2008)። ተጨማሪ ማስረጃዎችንም ከሚከተሉት ምንጮች ይመለከቷል። ዌይን ግሩደም፤ ስልታዊ ነገረ መለኮት፤ ቅጽ 1፤ የመጽሐፍ ቅዱስ አስተምህሮ መግቢያ (አዲስ አበባ፤ ኤስ አይ ኤም፤ 2003) ገጽ 656-65፤ ኮሊን ማንስል፤ ትምህርተ ክርስቶስ (አዲስ አበባ፤ 1999) ገጽ 200-2፤ L. Berkhof, Systematic Theology (Grand Rapids: Eerdmans, 1979), 340-43.

[28] ኮሊን ማንስል፤ ትምህርተ ክርስቶስ፤ ገጽ 202።

[29] Stott, The Cross, 179-81.

[30] John Piper, The Passion of Jesus Christ: Fifty Reasons Why He Came to Die (Wheaton: Crossway, 2004) የሚለው መጽሐፍ በጌታ ኢየሱስ ሞት የተገኙ 50 ትሩፋቶችን በዝርዝር ያቀርባል።

[31] Bowman Jr., Word-Faith Controversy, 176.

[32] ዝኒ ከማሁ፤ ገጽ 70።

Read 14224 times Last modified on Thursday, 01 December 2016 04:28
Paulos Fekadu

ጳውሎስ ፈቃዱ ባለ ትዳርና የሁለት ልጆች አባት ሲሆን፣ በሞያው መምህር ነው። በነገረ መለኮት እና በኮምፒውተር ሳይንስ፣ ከኢትዮጵያ ሥነ መለኮት ድኅረ ምረቃ ትምህርት ቤት (EGST) እና ከአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የማስተርስ ዲግሪዎች ያሉት ጳውሎስ፣ እግዚአብሔርን በአእምሮውም ለመውደድ የሚሻ አማኝ ተደርጎ ቢወሰድ ይመርጣል።

Email This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it.

Nahu's Corner

 

 

 

.

Right Now

We have 20 guests and no members online

About Us

Semayawi Thought is an online magazine published in Amharic and English, focused on contents to spiritual and personal growth.