በዚህ ጉዳይ ላይ “ጊዜው ራሱ መጨረሻቸውን ያሳያቸዋል … እኔ ምን አንጨረጨረኝ…” የሚል አቋም ነበረኝ:: ግን እየቆየ ሳስበው … “እኔ ካላገባኝ ማን ሊያገባው ነው?...” ወደሚል አቋም መጣሁ!!! ስለዚህ ይህ ጉዳይ በእጅጉ መስተካከል የሚገባው ሆኖ ተሰማኝ … ለሚመለከተውም ቢሰማም - ባይሰማም እናገራለሁ!!!
የማወራው ስለኳስ አይደለም ፤ ፖለቲካም የኔ አጀንዳ አይደለም፤ ስለአንድ ግለሰብም ብዕር ማንሳት አልወድም … :: ስለምን እንደምናገር ራሱ ሀሳቡ ይነግራችኋል::
ሀገርን እንደ ሀገርነቷ … ባህልና ቅርሶቿን ፤ ትውፊትና እምነቷን ፤ ወግና ስርዓቷን … በጠቅላላው ማንነቷን አክብረንና ጠብቀን እስካልሄድን ድረስ የሚመጣባትን የማንነት እጦት እንዲሁም በሌሎች የመዋጥ ችግር ሀላፊነቱን እኛው ነን የምንወስደው:: በተለይ ደግሞ ፈሪሀ እግዚአብሔር ያለን ሰዎች በምድር የሚደረግ ነገር ሁሉ ያገባናል!! እምነታችን እንደዛ ይላላ!!
እንዲህ ያልኩት በክርስትና “አስተማሪነት” እና “ነቢይነት” ስም የሚካሄዱ “አጓጉል” ድርጊቶች በሀገራችን እየገቡና ስር እየሰደዱ ስለተመለከትኩ ነው::
በመጀመሪያ ደረጃ … የክርስትና መነሻውና መደምደሚያ ሀሳብ ምንድነው የሚለውን ሳነሳ -
“ ሰው ሁሉ ኃጢአትን ሰርቷል ፤ የእግዚአብሔርም ክብር ጎሎታል ፤ በስራውም መፅደቅ ተስኖታል:: ስለዚህ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን የአለምን ህዝብ ለማዳን ሲል ለሞት አሳልፎ ሰጠው:: ኢየሱስም (አንድያ ልጁም) ሞትንና ኃጢአትን ድል ነሳ!!! እንዲሁም ደ’ሞ ይህንን እውነት የሚያምኑትን ድል ነስተው ይድኑ ዘንድ “እንዲሁ” (በባዶ ፥ በፀጋው) በስራ የሚገለጥ እምነትን ሰጣቸው!! ስለዚህም በከንቱ (በባዶ ፥ በፀጋው ፥ ያለምንም ክፍያ) የተቀበሉትን ፀጋ ለሌሎችም እንዲሁ እንዲያካፍሉ እግዚአብሔር ለዳኑት (ለሚድኑት) ያለው የመኖር አላማ ነው …”
ይህ ከላይ ያለው የማንኛውም ክርስቲያን (የክርስቶስ ተከታይ ፥ ክርስቶሳዊ) እምነት ነው!! (በክርስትና ውስጥ ብዙ ክፍፍሎች እንዳሉ ሳንረሳ …)
ታዲያ ይህን ሁሉ ካልኩ በኋላ … ከተለያዩ ሀገራት ተለቃቅመው የመጡ ፤ ክርስትናንም ሆነ የሀገሪቱን ህግና ስርዓት የሚፃረሩ ኑፋቄ “ስርዓቶችን “ … እንደሚመለከተው የእምነቱ ተከታይ .. እንዲሁም እንደሀገሪቱ ነዋሪና ተቆርቋሪ … ላወግዝ ነው ዛሬ የተነሳሁት!!!
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በአንዳንድ ግለሰቦች አስተባባሪነት ከክርስትና እምነት ውጪ የሆነ “አገልግል” ይሁን “አገልግሎት” ያልለየ ልምምድ ብቅ ብሏል!! ከነፍስ መዳን ጋር ያለውን የክርስትና ትስስር ንዶ “እንብላው” የሆነ፤ ተስፋው በምድር ላይ ብቻ የተወሰነና በስመ ክርስትና ትውልድን መበዝበዝ እቅዱ ያደረገ ተልካሻ “አገልግሎት” ነው ይህ እያወራሁ ያለሁት!!!
ከዚህ “አገልግሎት” ውስጥ የሚከተሉት ተጠቃሽ ናቸው -
- ፈውስን ፈልገው ለሚመጡ የእምነቱ ተከታዮች (ምዕመናን) ለአገልግሎቱ ገንዘብ ማስከፈል / ወይ በአንድ ፊቱ ሆስፒታል ሆኖ ለሀገሪቱ ታክስ አልከፈለ …. /
- “ትንቢት” ለመናገር አሁንም አስቀድሞ ገንዘብን ማስከፈል / ምን ትንቢት ነው ኢሄ - ሟርት ነው እንጂ … /
- “አስተማሪ” ተብዬዉም ጥሩ ገንዘብ ወደሚከፍለው ብቻ መሮጥ
- ትምህርቶቹም ሆነ ትንቢቶቹ ከቦርጭ ፥ ከመላጣነት ፥ ከባንክ አካውንት ገንዘብ መዳጎስና መሰል “የሸቀጥ” ጉዳዮች ጋር የተያያዙ ናቸው
መንግስት በዚህ ጉዳይ ላይ ያለውን አቋም አላውቅም!! ግን ታክስ የማይከፍል የዉጪም ሆነ ያገር ውስጥ ግለሰብ ወይ ገንዘብ የማያገኝ መሆን አለበት ፥ አለበለዚያ …. / ይህኛውን ማውራት ቦታው አይደለም ብዬ ልለፈው ሂ.ሂ.ሂ. /
በክርስትና እምነት ተከታዮች በራሳችን ግን … መፅሀፍ ቅዱሳችን - እንዲህ ዓይነት ሰዎች ልክ እንዳልሆኑና እግዚአብሔር እጅግ እንደሚቃወማቸው ይነግረናል -
ሚኪ. 3 ፥ 9 – 11
“…ፍርድን የምትጥሉ ቅን ነገርንም ሁሉ የምታጣምሙ እናንተ የያዕቆብ ቤት አለቆችና የእስራኤል ቤት ገዦች ሆይ እባካችሁን ስሙ :: ጽዮንን በደም ፥ ኢየሩሳሌምንም በኃጢአት ይሰራሉ:: አለቆችዋ በጉቦ ይፈርዳሉ ፥ ካህናቶችዋም በዋጋ ያስተምራሉ ፥ ነቢያቶችዋም በገንዘብ ያምዋርታሉ ፥ከዚህም ጋር :: “እግዚአብሔር በመካከላችን አይደለምን? ክፉ ነገር ምንም አይመጣብንም” እያሉ በእግዚአብሔር ይታመናሉ:: ስለዚህ በእናንተ ምክንያት ጽዮን እንደ እርሻ ትታረሳለች ፥ ኢየሩሳሌምም የድንጋይ ክምር ትሆናለች…”
ከላይ ያለው የመፅሀፍ ቅዱስ ክፍል ግልፅ ሀሳብ ያነሳል!! በነፃ የተቀበሉትን የፀጋ ስጦታ በክፍያ የሚቸረችሩትን ሁሉ የሚናገር ነው :: እንደውም በሀገሪቱ ላይ ለመጣውና ለሚመጣው ውድቀት ተጠያቂም ያደርጋቸዋል!!! ….
እንግዲህ ዛሬም ተመሳሳይ ሟርተኞችን በየመድረኩና በየሚዲያው እያየን ነው!! ይህ ዓይነት ልምምድ ግን የክርስትናም የሀገራችንም ስርዓት የማይደግፈውና በሀገሪቱም በእግዚአብሔርም የሚነቀፍ ነው!!
ህዝቡም ይህንን አውቆ እንደዚህ ዓይነት ስርዓተ-አልበኝነትን በእጅጉ ሊቃወም ይገባል!!! ክርስቲያኑ ማህበረሰብ ደ’ሞ እንዲህ ዓይነት ኑፋቄን ከየእምነት ድርጅቶቹ አውጥቶ መጣል ይገባዋል እላለሁ!!!