ቀደምት ሆነው በአዲስ አበባ ውስጥ ከተመሠረቱት ስድስት የመሠረተ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን አጥቢያዎች መካከል አንደኛ የሆነችውና በመሃከለኛው የአዲስ አበባ ክፍል ላይ የምትገኘው የቀበና አጥቢያ መሠረተ ክርስቶስ ቤተክርሰቲያን በአምልኮ ቦታ ላይ በተለያዩ ጊዜያት የተለያዩ ችግሮች የገጠሟት ሲሆን ይህም ችግር መደበኛ የእሁድ አምልኮ ፕሮግራሟን እስከ ማቋረጥ የደረሰበትም ወቅት እንደነበር ፓስተር ዶክተር የምሩ ጥላሁን ገልጸውልናል፡፡ አጥቢያይቱ በቀበሌ አዳራሽ፣ በኖርዌጂያን ሚሽን አዳራሽና በቀድሞው የግብርና ሚ/ር አዳራሽ እየተዘዋወረች የአምልኮ ፕሮግራሞቿን ስታካሂድ ቆይታ በኋላ ግን በደርግ ዘመን ተወርሶ በነበረው በኦሎምፒያ መሠረተ ክርስቶስ ቤ/ክ ጸሎት ቤት ለማምለክ የሚያስችል ፍቃድ ስለተገኘ ከ 1986 - 1996 ዓ.ም. የቅዳሜና እሁድ ፕሮግራሞችን በዚያ ስታካሂድ እንደቆየች እና፣ ሆኖም ግን ምክንያቱ ባልታወቀና ፍትሐዊ ባልሆነ መንገድ በድጋሚ ስፍራዋን እንድትለቅ እንደተደረገችም ለመረዳት ችለናል፡፡
የኦሎምፒያን የጸሎት ቤት በህግ አግባብ ለማስመለስ ካላት ቁርጠኝነት እና ከበዛላት ከጌታ ጸጋ የተነሳ ከመሠረተ ክርስቶስ ዋናው ቢሮ እና ከአዲስ አበባ ክልል ቢሮ ጋር በመሆን እልህ አስጨራሽ ጥረት እያደረች እንደምትገኝና፤ ሆኖም የጸሎት ቤቷን የማስመለሱ ጉዳይ ቀላል እንዳልሆነ ለማወቅ ችለናል፡፡
በአሁኑ ጊዜ የመሠረተ ክርስቶስ ቤ/ክ ዋናው ቢሮ እያስገነባ ባለው ጅምር ህንጻ ውስጥ የአምልኮ ፕሮግራሞቿን እያካሄደች ቢሆንም ይህንን ህንጻ ለማጠናቀቅ ቢሮው በያዘው እቅድ መሠረት ስፍራው መለቀቅ ስላለበት በድጋሚ ከማምለኪያ ስፍራ ጥያቄ ጋር አጥቢያይቱ ትገኛለች፡፡ አጥቢያይቱ ባለችበት አካባቢ ካለው የቦታ ገበያ ውድነት የተነሳ የማምለኪያ አዳራሽ በግዢም ሆነ በኪራይ የማግኘቱ ነገር አስቸጋሪ ቢሆንም ይህንን የማምለኪያ ቦታ ጥያቄ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ለማቃለል የተለያዩ ቦታዎችን በማየት ለመግዛት ሙከራ በማድረግ ላይ እንደምትገኝ ለማወቅ ችለናል፣ ሆኖም የሚያስፈልገው የገንዘብ መጠን ግን ከአጥቢያዋ አቅም አኳያ ያልተመጣጠነ በመሆኑ ልዩ ልዩ የገንዘብ ማሰባሰቢያ ፕሮግራሞችን በመቀየስ እየተንቀሳቀሰች ትገኛለች፡፡ ስለሆነም ገቢ ለማሰባሰብ እና ለምክክር ቅዳሜ ሰኔ 6/2007 ዓ.ም. በሳሮማርያ ሆቴል ከቀኑ 11፡30 – 2፡30 የሚቆይ ፕሮግራም አዘጋጅታለች፤ የእግዚአብሔር መንግስት ጉዳይ እና የቤተክርስቲያን አገልግሎት ይመለከተኛል የሚል ሁሉ በፕሮግራሙ ላይ እንዲገኙ ጥሪዋን ታቀርባለች፡፡
በዕለቱ ወንድም ዳዊት ይስሃቅ በቃል፣ ወንድም ገዛኸኝ ሙሴ በዝማሬ እንደሚያገለግሉ ሰምተናል።
ለበለጠ መረጃ የሚከተሉትን ስልኮች ይጠቀሙ
0911-343134/0911-695045