አቶ ለማ ደገፋ የ LET ሚኒስትሪ መሥራች እና አገልጋይ ሲሆን ባለፉት አመታት በተለይም በገጠሪቱ የኢትዮጵያ ክፍል ያሉ ወንጌላውያን እና አገልጋዮች የአመራር ሥልጠና እንዲያገኙ በማድረግ ይታወቃል፡፡ ከዚህ ቀደም የተለያዩ መጽሐፍትን ያሳተመ ሲሆን በኤሌሌ ኢንተርናሽናል ሆቴል ተጋባዥ እንግዶች እና የቤተ ክርስቲያን መሪዎች፣ እንዲሁም የኢትዮጵያ ደራሲያን ማኅበር ፕሬዚደንት በተገኙበት አንድ የኦሮሚኛና ሦስት የአማርኛ በድምሩ አራት መጽሐፍት አስመርቋል፡፡
የመጽሃፍቱም ይዘት
- የሕይወት ዉቅር - 257 ገጾች ያሉት ሲሆን አንድ ሰዉ አምኖ የበሰለ ደቀ መዝሙር ወደ መሆን እስኪያድግ ድረስ ያለዉን አጠቃላይ ክርስቲያናዊ ሕይወትና ተግባርን ይዳስሳል። የተጻፈዉ ለአማኞች በሙሉ ሲሆን በዓይነቱም ሆነ በይዘቱ በአገራችን የመጀመርያ ነዉ፡፡ መጽሐፉ ዝርዝር የሆኑ የእምነት ዉቅሮችን የሚዳስሰዉን ያክል አንኳር የክርስትና ፈርጦችን አጉልቶ ያሳያል፡፡ ወንጌላውያን አማኞች በሙሉ በየቤታቸዉ ቢያጠኑት ለሕይወት ጤንነትና ለቤተ ክርስቲያን ዕድገት የላቀ አስተዋጽኦ ይኖረዋል፡፡
- Jiruuf Jireenya – 316 ገጾች ያለዉ ሲሆን በአፋን ኦሮሞ ለሚያገለግሉና ለሚገለገሉ አማኞች አዉዳዊ በሆነ መንገድ የተዘጋጀ ነዉ፡፡
- ከመሩ አይቀር ባለ 155 ገጽ መጽሐፍ ሲሆን እጅግ ጥልቅ የአመራር ጥበብን ይዳስሳል፡፡ በዓይነቱ የመጀመርያ ኢትዮጵያዊ የአመራር ነገረ መለኮት ነዉ፡፡ የአመራርን ምንነት፤ የመሪን ማንንትና የመሪን ድርሻ ያዳስሳል፡፡ በየትኛዉም ደረጃ ለሚገኙ መሪዎች፣ ለአመራር ተማሪዎች፣ አመራር ላይ ስልጠና ለሚሰጡ ተቋማት በሙሉ የሚሆን ነዉ፡፡
- ካደጉ አይቀር 220 ገጾች አሉት። ሰዉ ሲያድግ ሁሉ ያድጋል፣ ስኬታማ ሰዎች ኑሮን ከራሳቸዉ የጀመሩት ናቸዉ እያለ የሕወትን ሁለንተና ይዳስሳል፡፡ እንጀራን እንደ ተምሳሌት እየተጠቀመ እያዝናና ዉድ ስለሆነዉ የሰዉ ልጅ ሕይወት ያስተምራል፡፡ የተጻፈዉ ለወጣቶች፣ ለቤተሰቦችና ሰዉ ልማት ላይ ለሚሠሩ ሁሉ ነዉ፡፡
Semayawi Thought እንድታነቧቸው ይጋብዛል፡፡