ክርስትና ድሩም ማጉም እምነት ነው፡፡ በእግዚአብሔር ማመን፤ በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ ማመን፤ በመንፈስ ቅዱስ ማመን፣ በሙታን ትንሣኤ ማመን፣ በክርስቶስ ቤዛዊ ግብር ማመን ወዘተረፈ፡፡ በአጠቃላይ ክርስትና ዋልታና ማገሩ፣ መሠረቱና ውቅሩ እምነት ነው፡፡ የቃሉን ትርጓሜና ዳር ድንበር፣ የመሠረተ ሐሳቡን ስፋትና ጥልቀት እንዲሁም በርእሰ ጒዳዩ ላይ በሚቀርቡ መስመር የሳቱ ትምህርቶችና ልምምዶች ላይ ሒስ መሰንዘር፣ የዚህ ጽሑፍ መነሻም መድረሻም ነው፡፡ በአጭሩ ጽሑፉ ትምህርታዊና ዐቅብተ እምነታዊ ተልእኮ በመሰነቅ፣ ቃለ እግዚአብሔርንና ምክንዩን የጒዞ መስመሩ ያረገ ጽሑፍ ነው፡፡
ከቅርብ ዓመታት ወዲህ አንዳንድ የሃይማኖት መምህራን፣ እምነት ለሚለው ቃል የሚሰጡት ትርጓሜ እንዲሁም ለትርጓሜያቸው የቀመሩት ነባቤ ቃል፣ ግዘፍ ነሥቶ ገቢራዊ እንዲሆን የሚያደርጓቸው ጥረቶች፣ ክርስቲያናዊ ያለመሆናቸው ብቻ ሳይሆን፣ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እጅግ ብዙ ዝርክርክ ነገር እንዲፈጠር ምክንያት ሆኗል የሚል እምነት አለኝ፡፡ ጌታን እንደ ግል አዳኜ አድርጌ ከተቀበልሁበት ዘመን ጀምሮ፣ ቤተ ክርስቲያን በብዙ እንግዳ ደራሽ ትምህርቶች ስትናጥ፣ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ላልሆኑ ልምምዶች ሰለባ ስንሆን አይቻለሁ፡፡ ነገር ግን የእምነት እንቅስቃሴ እንደሚባለው ወልካፋ ትምህርት በቤተ ክርስቲያንን ያስነወረ፣ ከፍተኛም ውድመት ያመጣ ስሑት አስተምህሮ ያለ አይመስለኝም፡፡ “በዚህ ትምህርት የተነካካው ማነው?” ከሚለው ምርመራ ይልቅ፣ “ያልተነካካው ማነው?” የሚለው ጥረት ከብዙ አንጻር ድካምን የሚቀንስ ይመስለኛል፡፡ ከሊቅ እስከ ደቂቅ፣ በማወቅም ሆነ ባለማወቅ ለትምህርቱ ሎሌ አድሯል፡፡ ይህ አነጋገሬ እውነት ከሆነ፣ ይህ ጽሑፍ እንዲሁም ወንድም ምኒልክ አስፋው የሚያቀርበው ትምህርት እጅግ ወሳኝ ነው፡፡ ወገኖቼ ሆይ፣ ዐውደ ጥናቱን ከሙሉ ልብ እንድታነቡ በጌታ ፍቅር እጠይቃለሁ፡፡ ሚዛናዊናት የጐደለው ነገር ካለ እንደ ብርሃን ልጆች በግልጽነት እንወያይ፡፡ ጥያቄ የፈጠረባችሁ ነገር ካለ ያለንዳች ማቅማማት ለውይይት አቅርቡት፡፡ የዐውደ ጥናቱ ዐላማም ሆነ ግብ እኛን ወደ ቃሉ ማዕከላዊነት በመሳብ አምላካችን እግዚአብሔርን ማክበር ነውና፡፡
ሰንበት ትምህርት ቤት ውሎ የመጣ ወጣት እናቱ፣ “ልጄ ዛሬ ምን ተማራችሁ” ብላ ስትጠይቀው፣ “ስለ እምነት፤ ዛሬ የተማርነው ስለ እምነት ነው” ይላታል፡፡ “ስለ እምነት ምን ተማራችሁ”፣ “እምነት እንደማይሆን የተረጋገጠን ነገር ፈጽሞ ጨልጦ ማመን ማለት ነው፤ እንዲያውም ትክክል እንዳልሆነ የተረጋገጠውን ይህ ዐይነቱን ነገር ፍርጥም ብሎ ያለማመን ጥርጣሬና ምንታዌ ነው” እንዳለ አንብብያለሁ—ግነትና ድምቀት መጨመሬን ግን አልክድም፡፡ በተመሳሳይ መልኩ፣ አንድ የወጣት መሪ፣ “እኔ እግዚአብሔር ብሆን ኖሮ ነገሮችን ሁሉ ፍጹም ግልጽ በማድረግ፣ እምነት በሕይወታችን ውስጥ አንዳችም ፋይዳ እንዳይኖረው አደርግ ነበር” ማለቱ ትዝ ይለኛል፡፡ አንድ የእምነት እንቅስቃሴ መምህር ደግሞ፣ እምነት የሚለውን ቃል የተረጓመው በሚከተለው መልክ ነው፣ “እምነት ማለት ጒዳዩ በቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ ተጠቅሶ ባይገኝ ኖሮ፣ ቀልቡን ያልሳተ ጤናማ ሰው ሊሆን ይችላል ብሎ በጭራሽ የማይቀበለውን ነገር አምኖ መገኘት ነው”፡፡
በዚህ አካባቢ የሚኖሩ፣ “እኔ የእምነት እንቅስቃሴ መምህር ነኝ”፣ “እኔ የብልጽግና ወንጌል ሰባኪ ነኝ” እያሉ በግልጽ የሚናገሩ አንድ ኢትዮጵያዊ ሰባኪ፣ “ራይዝ ኤንድ ሻይን” በተባለ ቶክ ሾ ላይ ቀርበው እንዲህ ብለዋል፣ “ፋክትና ሪያሊቲ የተለያዩ ነገሮች ናቸው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ የሚናገረው ትምህርት ሁሉ ሪያሊቲ ነው፡፡ ኢየሱስ የኢያኢሮስን ሴት ልጅ ከሞት ሲያስነሣ፣ ተኝታለች ነው ያለው፤ ይህም ኢየሱስ ሞታለች የሚለውን ክዶታል፡፡ ተኝታለች ብሎ በመናገሩ ሪያሊቲውን ስለካደ ልጅቱ አልሞተችም፤ ነገር ግን ተኝታለች፡፡ ስለዚህ ኢየሱስ የሞተውን ሰው ሳይሆን ያስነሣው ያንቀላፋውን ሰው ነው”፡፡
እስካሁን ያየናቸው የእምነት ትንታኔዎች ትክክል ከሆኑ፣ እምነት እውር ድንብሩ የወጣ፣ ደመናፍሳውያኑ እንስሳት እንጂ አእምሮ የተቸረው ፍጥረት የማይቀበለው የወይዛዝርት ዋዛ ፈዛዛ ነው፡፡ አእምሮ ያለው ፍጥረት አእምሮ ቢስ ለመሆን ሲዳዳ፣ በምክንያትነት የሚያቀርበው ሰበብ (ተገን) ነው ማለት ነው፡፡ በርግጥ እምነት ማለት እነዚህ ሰዎች ያሉት ነገር ከሆነ፣ እምነት አሻሚ እንዲያውም ከምክንዩ ጋር ተጻራሪ የሆኑ ነገሮችን ለመቀበል በምክንያትነት የምናጣቅሰው የጥንቈላ ብትር ነው ማለት ነው፡፡ ስለዚህ አንድ ነገር እምነት ፈለገ ማለት ነገሩ አሻሚ ነው ወይም ነገሩን ለመቀበል አንዳችም እእምሮአዊ ማስረጃ የለም ማለት ነው፡፡
ይህ ጽሑፍ በሁለት መሠረታውያን ነገሮችን ይመረምራል:—
- እምነት ማለት ምን ማለት ነው?
- የእምነት እንቅስቃሴ አስተምህሮ ስለ እምነት የሚሰጠው ትንታኔ በቅዱሳት መጻሕፍት ሲፈተሽ በርክጥ ርቱዕ (ትክክለኛ) አስተምህሮ ነውን?