You are here: HomeOpinionsአባቶች ሲስቱስ?

አባቶች ሲስቱስ?

Written by  Monday, 14 May 2018 10:30

ወጣቱ ለአዲስ ነገር ያለውን ጥማት በማየት “ቅልብልብ፣ ለስሕተት አሠራር ክፍት፣ ለቋሚና ዘላቂ ነገር ራሱን የማይሰጥና ተለዋዋጭ” አድርጎ የማየት አዝማሚያ በየትኛውም የዓለም ክፍል ያለ ነው ብዬ አስባለሁ፡፡ የዚህች አጭር ምልከታ ዐላማ፣ የወጣቱን መንፈሳዊ ጤንነትና አካሄድ ማጠየቅ ሳይሆን፣ በዕድሜ ስለጠኑ ግን ደግሞ እውነትን ስለተቀሙ፣ በዘመን ዕድሜ ቆይታ የእውነትን መንፈስ አውልቀው ሐሰትንና አሠራሩን በአጭር ስለታጠቁ፣ በቊጥርም እየበዙ ስላሉ፣ ስለ “ትናንት አባቶች” የዛሬ ስሑታን ነው፡፡ እንደ መርዶ ያህል ነው፤ ሌላውን በመምከሪያ ዘመናቸው የሚመከሩ፣ ሌላውን እንደ እረኛ መጠበቅ የሚገባቸው፣ ግን በዕድሜያቸው ሙጣጭ ላይ ሊጠበቁ ስለተገባቸው የዕድሜ ባለጸጋዎች ጕዳይ ነው በዚህ ጽሑፌ የማወሳው፡፡ ምልከታዬን ከጥንቱ ዘመን ታሪክ እጀምርና ወደ ዘመናችን አመጣለሁ፡፡

 

ምዕመኑ! መሪውስ?

ከሰሜን አፍሪካዊቷ አገር ካርታጎ (የዛሬዋ ቱኒዚያ) የተገኘው ቅዱስ ስጵሪያኖስ (Cyprian)[1] በምድር ኑሮው ፍጻሜ ለጌታ ታማኝ ምስክር ሆኖ በሰማዕትነት ያለፈ፣ የቤተ ክርስቲያን መሪ እና (አወዛጋቢነቱ እንዳለ ሆኖ) ልከኛ የነገረ መለኮት ሰው ነበር፡፡ በቄሣር ዳሲዮስ (Dacius) አገዛዝ፣ በ249 – 251 ዓ.ም. የተነሣውን እጅግ አስከፊ የስደት ዘመን ቅዱሳንን በማጽናት ያገለገለ፣ ከስደቱ ዓመታት በኋላም በወጣው የአምስት ዓመት የሰላም ጊዜ ውስጥ ለቤተ ክርስቲያን ልክ ነው ብሎ ያመነበትን መመሪያዎች የሰጠና ቤተ ክርስቲያንን የጠበቀ ሰው ነበር፡፡

 

በእነዚያ ዓመታት ሊያስተካክል ከሞከረው ጕዳይ አንዱ ከእምነት ወደ ኋላ ስለተመለሱ ሰዎች ነበር፡፡

 

የዳሲዮስን ዘመነ መከራ የተሰቀቁ ጥቂት የማይባሉ ክርስቲያኖች ለጣዖታት መሥዋዕት ማቅረባቸውን የሚገልጽ ሠርተፊኬት (libelli) ወስደው (ወድደው/ተገደው ለጣዖታት መሥዋዕት ካቀረቡ በኋላ) ወይም ደግሞ (መሥዋዕት እንዳቀርቡ በማስመሰል ሠርቲፊኬቱን) ገዝተው ሕይወታቸውን አትርፈው ኖሯል፡፡[2] የሰላሙ ጊዜ ላይ ታዲያ፣ ሁሉም ከተደበቀበት ሲወጣና የቤተ ክርስቲያን ሕንፃ በሮች ሲከፈቱ፣ እነዚያ “ተንሸራቶችም” መጥተው አገልግሎት ፈለጉ፡፡ ነገሩ አወዛገበ፡፡ አንዱ ወገን፡- “ጌታን ለሕይወታቸው ሲሉ የለወጡትን አንቀበላቸው፤ ለቀጣዩ ጊዜ መልካም ምሳሌነት የለውም” ሲል፣ ሌላኛው ወገን ደግሞ፡- “የሰው ድካም እዚህም ድረስ ነውና ያለ ምንም ቅድመ ሁኔታ እንቀበላቸው፤ ተመልሰው ወደ እኛ መምጣታቸው በራሱ ወደ ጌታ መመለሳቸው አይደለምን?” ብሎ ተከራከረ፡፡[3]

 

ስጵሪያኖስ የእነዚያን ምዕመናን ወገኖች “ፈሪነት” አልወደደውም፤ ቢሆንም ግን በንስሓ አስፈላጊነት ደግሞ ያምናል፡፡ ለዚህም ነው “ይበጃል” ያለውን መልስ ጸንተው በቆሙ አባቶች (ጳጳሳትና ቀሳውስት) ሕይወት ውስጥ ያገኘ የመሰለው፡፡ በዚያ መከራ ጊዜ ጽኑኣን የነበሩ ወንድም-አባቶችን ዋቢ አድርጎ ስለ ጸጋ ብርታት አስተማረ፤ እነዚህ ብርቱዎቹ እነዚያን ደካሞች በእምነት እንዲጸኑ እንዲጸልዩላቸውና በንስሓቸው እንዲረዷቸው መከረ፡፡ ሐሳቡ በአብዛኛው ዘንድ ተቀባይነት አገኘ፡፡ ነገሩ ʻንጹሓንና እውነተኛ አባት-መሪዎች ስላሉ … ለምዕመናኑ እንራራʼ ይመስላል፡፡

 

የኋላ ችግሩስ ምንድን’ነው? የዳሲዮስ ዘመን የምዕመናኑን ታማኝነት የፈተነ ቢሆንምና “በአባቶች” ንጽሕና የተተገነ መልስ ቢሰጠውም ከተወሰኑ ዓመታት በኋላ ለመጣውና አባቶች ራሳቸውን ላጠቃው ችግር ግን መፍትሔ አልነበረውም፡፡ የዲዮቅላጥያኖስ (Diocletian) ከበድ ያለ ስደት (በተለይ 286 – 305 ዓ.ም.) “ምእመኑን” አልፎ “አባቶችን” ያንበረከከ ነበር፡፡ “የምታስተምሩበትን መጽሐፍ ቅዱስ አስረክቡ ወይም ሞታችሁን!” ለሚለው አዋጅ፣ አንዳንድ አባቶች “‘መኖር ደግ’ ብለው መጻሕፍትን ለእሣት ሰጡ” ነበር የቀረበባቸው ክስ፡፡[4] ከስደቱ በኋላ ሌላ የሰላም ዘመን ሲመጣ የሳተውም ያልሳተውም፣ ለጌታ የመሰከረውም የካደውም፣ ለእምነቱ እጁ የተቆረጠውም በእጁ መጻሕፍት ያስረከበውም… እኩል ለአገልግሎት አትሮኖስ (ፑልፒት) ላይ ቆሙ፡፡

 

በእውነት አደናጋሪ ጊዜ ነበር፡፡ ያኔ “የምዕመኑን ድካም በመሪዎች ጤንነት እንፍታ” ተባለ፣ የአሁን ዘመን ተፍገምጋሚዎች ደግሞ “አባቶች” የሚባሉት ሆኑ፡፡ አባቶች ሲስቱ በምን ይዳኙ? ማንስ ይመልሳቸው? ማንንስ ይስሙ? ማንስ ማንን ይዳኝ? የስጵሪያኖስ ‘የቅዱሳት ምሥጢራት ነገረ-መለኮት’ (Sacramental theology) ትምህርት ለዚህ መልስ ያጥረዋል፡፡ ጉዳዩ ታዲያ በሌላ ሰፋ ባለ ክርክርና ትምህርትም የታለፈ ቢመስልም የካርታጎ ሊቀ ጳጳስ/መሪ ሆኖ የተሾመው ዶናተስ (Donatus) እነዚህን “አባቶች”ን ባለመቀበል ተሰለፈ፤ ይህ ነውና ቤተ ክርስቲያንም በብርቱ መከፋፈልና ማነከስ መኻል ዕድሜ ዘመኗ የረዘመ መሆኑን ያለመጥቀስ አይቻልም፡፡ የችግሩ ጦስ ግን የት-የለሌ ነው፡፡ የ”ዶናተስ ተከታዮች” የሚባሉት የተስፋፉበት የሰሜን አፍሪካ ግዛቶች ኋላ ላይ የክርስቶስ ትምህርት በሌላ እንግዳ ትምህርት በቀላሉ ፈጥኖ ለመወረስ በቅቷል፤ ይህ ከ“አባቶች” የተነሣ የተከሰተው ስብራት በታሪክ ውስጥ እንደ አንድ ምክንያት ተቆጥሯል፡፡ የካርታጎ ክርስቲያኖችን ከ“ዐመፃቸው” መልሶ ለማንበርከክ “የቤተ ክርስቲያን ጭከና ከተሞላበት ጡጫ” ተጠቅማ ይሆናል፤ እነርሱም ታዲያ በመንግሥት ኀይል ከተደገፈችው ቤተ ክርስቲያን ይልቅ፣ ባዕድ የዐረብ ተስፋዎችን መከታ (በተላላነት) ፈለጉ፣ “የክርስትናም ነፍስ ከዚያ የአፍሪካ ምድር ቀስ በቀስ ወጣ” ይላሉ የግራውን የቀኙን ያዩና የተቹ፡፡ በርግጥም ለዚያ አካባቢ የአፍሪካ ምድር ክርስትና ጥሩ ድምዳሜ አልሆነም፡፡

 

አባት ውርስ” ተግዳሮቶቻችን

በእምነት ጽንተው ለሌላው ብርታት የሆኑ አባቶች ብዙ እንዳሉ ሁሉ፣ ለቀጣዩ ትውልድ መጓጓዣ ድልድይ ሰባሪ፣ ፍርሀትን አሰናቂ “አባቶች”ም ነበሩ፡፡ ክርስትናን ኖረው ጌታን ያስከበሩት ብዙዎች እንዳሉ ሁሉ፣ ለሙጣጭ ዘመናቸው ብለው ያዳናቸውን ጌታ የካዱ ነበሩ፡፡ የታሪክ ገጾች ስለዚህ የሚሉት ብዙ አላቸው፡፡

 

ለእምነት እውነት መስክረው ያለፉ የዕድሜ ባለጸጋዎች እንዳሉ ሁሉ፣ የስሕተት ትምህርት አፍላቂና አድናቂ ዕድሜ ጠገብ ሽማግሌዎችም ነበሩ፡፡ ለቃሉ እውነትና ለቤተ ክርስቲያን ጤንነት ራሳቸውን የሰጡ እንደ ነበሩ ሁሉ፣ እውነት ያልዘለቃቸውና ከጊዜ ብዛት የአዳኛቸው ብርሃን የደበዘዘባቸው ዕድሜ ጠገብ ሰዎችም ነበሩ፡፡

 

መሳትና በስሕተት ጎዳና መገኘት የዕድሜ ጕዳይ የሆነ አይመስልም፡፡ “ወልድ ፍጡር” ባይ ቄስ አሪዮስ፣ መንፈስ ቅዱስን “ኀይል ብቻ” ባይ መቅዶንዮስ፣ የኢየሱስን ምንታዌነት (ሁለትዮሽ) ያስተማረው ፓትሪያርክ ንስጥሮስ … ዕድሜም ሆነ በዕድሜ ያገኙት ትምህርት ያልመለሳቸው ስሑታን “አባቶች” ናቸው፡፡ መራር እውነታውን ስንጋፈጥ እነዚህና የመሳሰሉቱ ቁልል ዕድሜ ከስሕተት ያልጠበቃቸው፤ የሽምግልና ዕድሜያቸውን የእርጅና ያደረጉ ነበሩ፡፡

አይጣል ነው እንጂ ነገሩስ እውነት ነው፤ አባቶች”ም ይስታሉ፡፡

 

መጽሐፍ ቅዱሳችን ስለ ቡሩካን አባቶች በሰፊው ይተርካል (ዕብ. 11)፤ በዚያው አንጻር ደግሞ ለብዙዎቹ የሕዝቡ አለቆችና መሪዎች ብርቱ ተግሳጽ በነቢያቱ መጻሕፍት ብዙ ገጾች ላይ ታነብባላችሁ፡፡ ሕዝቡን ጣዖት ማምለክ ያስተምሩ የነበሩ እነማን ናቸው? “አንገተ ደንዳና የሕዝቤ መሪዎችና ሽማግሌዎች” የተባሉትስ? ሕዝቡን ያስቱ የነበሩ ነቢያትና ደጋፊዎቻቸው ያው ዕድሜ ጠገብ ካህናትና መሪዎች አልነበሩምን? ኤርምያስንስ ያስደነገጠው ይኸው አልንበረምን? የሚያስፈራና የሚያስደነግጥ ነገር በምድሪቱ ላይ ሆኗል፤ ነቢያት በሐሰት ትንቢት ይናገራሉ፤ ካህናት በነቢያቱ ምክር ያስተዳድራሉ፤ ሕዝቤም እንዲህ ያለውን ይወድዳሉ…” (ኤር. 5፥30-31)፡፡

 

ሰው ከእውነት ሲወዳጅና በእግዚአብሔር ብርሃን ሲጎበኝ ይህም እስከ ፍጻሜ እንዲያድግ አውቃለሁ፤ እንደነዚህ ዐይነቶቹን ማክበር ለበረከት መሆኑንም በሙሉ ልቤ አምናለሁ፡፡ አሳሳቢው ነገር ግን ዕድገታቸውን በስሕተታቸው የቆረጡና የዕድሜያቸው ድምድማት የውርደት ያደረጉ አባቶች ጥቂት ያለመሆናቸው ነው፡፡

 

ለእምነት ምሳሌ የማይሆኑ ስተው የሚያስቱ ነበሩ፤ አሉ፡፡ የመጽሐፍ ቅዱስም ሆነ የታሪክ ገጾች “ምራቅ ዋጥ ያደረጉ” የሚባሉና ዕድሜ ቸርነቱን ያልነፈጋቸው ሰዎች፣ ከእውነት ጎዳና ወጥተው የጌታን መንገድና ስም ያስጎደፉ ነበሩ፤ አሉ፡፡

 

ዛሬም የእኛ ዘመን አንዱ ተግዳሮት የአባቶችና አባት የሚሆኑ ሰዎች ዕጥረት ብቻ ሳይሆን፣ ገሚሱ በከረረ መንገድ ስሕተትን በመደገፍ የመሰለፍ፤ ከሐሰተኞች ጋር ትከሻ ለትከሻ የመግጠም፤ የጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን ወንጌል ለማጣመም የአንበሳ ድርሻውን ለመውሰድ ጎንበስ ቀና የማለት ነው፡፡ “ይህስ ለምን ይሆናል?” ብሎ የሚጠይቅ የሚያገኘው መልስ “የምን ታመጣላችሁ!” እልህ መስሏል፡፡ ዕብሪት “ወጣቱን ብቻ ያጠቃል” ብሎ የሚያስብም ካለ ወደ ወንጌላውያን ዘንድ ቢመጣ ጉዳዩን ተገላቢጦሽነት የሚረዳው ርቆ ሳይሄድ ነው፤ ዕብሪት የተሞሉ አረጋዊያንም ከነስሕተት ትምህርታቸው… እንደ በፊቱ ላይደበቁ… እነሆ በገሃድ አደባባይ ውለዋል፡፡

 

ሁለተኛውም ተግዳሮት፤ ራሳቸው “አባቶች” የተባሉቱ የስሕተት ትምህርት አራማጅነትና የተሳሳቱ ትንቢቶችን አምጪ ሆኖ ነጥሮ መውጣት ነው፡፡ ከብዙ ወራት በፊት ይህን ጽሑፍ በማጠናክርበት ወቅት[5] ለአዲስ ዓመት ዋዜማ የመልካም ምኞት መግለጫዎችና ምትሕታዊም ሰዋዊ ትንቢቶች እየፈሰሱ ነበር፤ ግማሹ “የስሕተት ሠርቶ ማሳያ” ዐይነት ነው፡፡[6] ቄስ ቶሎሳም በፍጹም ስሜት ሆነው ለምድራችን ርግማንና ያለ መባረክ ምክንያት የሆነውን ዐፄ ኃይለ ሥላሴን እንዴት እንደበደልን “ከእግዚአብሔር” ስለተቀበሉት መልእክት ያስተላልፋሉ፡፡ የንስሓ ጥሪው የብዙዎችን ልብ ሳይነካ አልቀረም፤ አጠያያቂው ጉዳይ ግን የአምላክን ስም ጠርተው ለዋቢነት ማቆማቸው ነው፡፡ “ይመስለኛል”፣ “ይህን ነገር ብንተገብረው ለምድሪቱ ጥሩ ነው” ቢሉ ደግ ነው ከሚሉ ጋር እስማማለሁ፡፡ አንድ በእሳቸው ዕድሜ ያሉ ብርቱ ጸሐፊ[7] ከዚህ በፊት የንጉሡን መውደቅ ከጴንጤቆስጤያዊ ታሪክ ጋር አዛምደው የዐፄውን “ልበ ደንዳናነት” ትረካ አስነብበውን ነበርና ላስተዋለው ስለዚህኛው “የእግዚአብሔር መልእክት” ሌላ ግርምት ፈጣሪ ነው፡፡ ዐሥራ ምናምን ዓመታት “ከእግዚአብሔር ያገኘሁት” ያሉትን መልዕክቶቻቸውን የነገሩን እኚህ እውቅ ሰባኪ በወንጌላዊያን ዘንድ የነበራቸውን ክብረት መናድ ከጀመሩ ውለው አደሩ፤ ጉዳያቸውም ስለ “አባቶቻችን” ማፈር የጀመርነው ጕዳይ እንዲህ በዋዛ የሚያበቃ አለመሆኑን አስረጅ ሆኗል፡፡ ይህችም ጽሑፌ በዚህ ጕዳይ የመጨረሻው ላይሆን ነው ማለት ነው፡፡

 

ባለፈው ጊዜ በወጣው የኢትዮጵያ ወንጌላውያን አብያተ ክርስቲያናት ኅብረት መግለጫ ላይ የተጠቀሱትን የስሕተት ትምህርቶች የሚያራምዱና የሚያራግቡ፣ ሐሰተኞችንም በሁሉም ዘርፍ የሚያበረታቱ የዕድሜ ባለጸጎች በብዙ አደባባዮች አላያችሁምን? የሰው ተኮሩ የእምነት እንቅስቃሴ “ወንጌል” አሠልጣኝ ተቋም በምድራችን የከፈቱና በገንዘብ የሚደግፉ፣ “መርዘኛ” ትምህርትና መምህራንን አፍላቂ ቪክትሪ “የሥነ መለኮት” ትምህርት ቤት በኢትዮጵያ ያቋቋሙት ዲሲ የምትገኘው የኢትዮጵያውያን ቤተ ክርስቲያን (ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያን ኢቫንጀሊካል ቸርች) ዕድሜ ጠገብ መሪው መጋቢ ፓ/ር አንፍሬ አሊጋዝ መሆናቸውን እያወቀ፣ “በምን አገባኝ”ም መንፈስ ያለፈ ጥቂት አይደለም፡፡ ትምህርት ቤቱ ግን በግልጽ የእምነት እንቅስቃሴን ከሚያስፋፋው የኦራል ሮበርትስ ተቋም ጋር መተሳሰሩን፤ ትምህርቱም በዚህ የስህተት ትምህርት መቃኘቱን እንኳን የቀረቧቸው[8] የሩቆቹም ያውቃሉ፡፡ ይኸዉ ሌላው፡- “ሰው መንፈስ ነው” በማለት በአደባባይ የሐሰት ትምህርትን ያወጁና ከ“መናፍስት” ጎራ ራሳቸውን ያስቀመጡት ቄስ ቶሎሳ ጉዲና ተከብረው ሊያስከብሩን ይገባ የነበረ አረጋዊስ አይደሉምን?[9] በኢትዮጵያ “ለመጀመሪያ ጊዜ በመንፈስ ቅዱስ ተሞልተው ልሳን የተናገሩ” የተባለላቸው የቨርጂኒያዋ የጸጋ ቤተ ክርስቲያን መጋቢ ዓለሙ ዘለቀ በዚሁ የእምነት እንቅስቃሴ ጎራ ራሳቸውን በወዶ ገብነት አልመደቡምን?[10]  

 

በዐሥራት በኩራትና ስጦታ የጉዞ ወጪያቸውንም እየሸፈኑም ቢሆን ከጎናቸው የቆሙት የዲሲ፣ የአትላንታና ቨርጂኒያ “ቤተ ክርሰቲያኖቻቸው” ምዕመን/አገልጋዮች ስለእነኚህ አረጋዊ “አባቶቻቸው” ተደጋጋሚ ጥፋት “በእውነት ምን ይሰማቸው ይሆን?” እላለሁ፡፡ የእነዚህ ግለ ሰቦችን ዐላማ በገንዘባቸው እየደገፉ በስንት መከራና የደም ዋጋ የተገነባውን የኢትዮጵያ ወንጌላዊ ክርስትና እምነት በተባባሪነት ከመሠረቱ ንደው የሚያስንዱ፣ ለእንዲህ ላሉ ግለ ሰቦች ፈቃድ ተገዢ አባላትና አግልጋዮች፣ በርግጥ በእግዚአብሔርና በሰው ፊት የማይጠየቁ መስሏቸዋል፤ ግን ይህ ሊሆን ፈጽሞ አይችልም::

 

ሦስተኛውና የክርስትናችን ፈተና ሆኖ ዛሬ ዛሬ ብቅ እያለ ያለው በሽታ በሽምግልና ስም የሚደረግ “ሁሉን እኩል እንቀፍ” ባይነት፣ “ሰይጣንንና እግዚአብሔርን እናሰታርቅ ባይ ‘ክርስቶስ ሰምራዊነት’” ነው፡፡[11] የተሰጣቸው ብርሃን ቢደበዝዝባቸው ጊዜ “ቅዱሱን ከርኩሱ” ለማግባባትና ለማጋባት ጎንበስ ቀና ማለት ድሮም ነበር ብንልም እንኳ፣ ዛሬ ግን መባሱን መደበቅ አልተቻለም፡፡ እነዚህ፡- በፍቅር ስም የመንፈሳዊውን ሁለት ተቃራኒ ዓለማትን እንኳ ለማስታረቅ የሚታትሩ፣ እውነት ተናጋሪውን “ፍቅር ዐልባ” በማለት እያመካኙ የሚኮንኑ እና “እውነተኛ ፍቅርን” ራሳቸው ከሚያዜሙለት “ልዝብ ፍቅር” ጋር አስተያይተው ሰማያዊውን እምነት መያዝ የሚያቅታቸው ናቸው፡፡ ለዚህ “ስለ ፍቅር … በስመ አብ ይቅር”[12] ባይ ተረት ተታሎ ማታለል፣ ተላልፎ መሰጠት ማለት ከላይ ወዳነሣሁት የመጀመሪያው የተግዳሮት ጎራ ውስጥ ለማግባት ማንደርደር ነው፡፡ ቀርቤ ያየኋቸው እንዲህ ያሉ “አባቶች” ፍላጎትና ያልተደበቀው ዐላማቸው ስሕተተኞችን መመለስ ሳይሆን (በአካል እዚህ) በሃሳብ ከዚያው ጎራ ተሰልፈው “እንደግፋቸው፣ እንቀበላቸው፣ ወንድም/እኅት እንበላቸው” ባዮች ናቸው፤ ይኸው ነውና መንገዳቸው ግባቸውን አልሳትነውም፡፡  

 

ለምን?” ተብሎ ይጠየቃል!

እንደ እኔ ዕይታ ከሆነ፣ ቢሆንላቸው የኢትዮጵያ ወንጌላውያን አማኞች አባቶችን የሚያከብሩ ናቸው፡፡ “ቢሆንላቸው” ማለቴ ሽማግሌው ዕድሜን ከእውነት ጋር ይዞ ቢገኝ ሕዝቡ እነሱን ማክበር አይከብደውም ለማለት ነው፡፡ ባህሉም፣ መጽሐፍ ቅዱሱም ያንን ይፈቀዳል፤ ያበረታታል፡፡ እንድንሰማቸውና እንድንታዘዛቸው በክብር ያሉትን የሰጠንን እግዚአብሔርን እናመሰግናለን፡፡ እነዚህን በፍቅር ልንይዛቸውና ልንባረክባቸው ይገባል፡፡

 

ግን ደግሞ እንደ ድንገቴ የወረደብን ዱብ ዕዳ ባይሆንም፣ መልካም አባት የሚሆኑና ሆነው ሊገኙ የሚ’ወዱ ቊጥራቸው ከምድሪቱ ላይ (ከቤተ ክርስቲያን ውጪ) መሳሳቱ አሳሳቢ ሆኗል፡፡ ግማሾቹ ተርፈው አስተዋይ መካሪ ሆኑ፤ ሆነና በሃገሩ ሽማግሌ አላጣንም፡፡ ስለሌሎቹ “አንዳንዶቹ” ፍርሀቴ ዕድሜ በመጨመሩ ተሳክቶላቸው ይሆን ይሆናል እንጂ አሁንም አርቆ አሳቢ ልቦና የበዛላቸው መሆኑን ርግጠኛ አልሆንኩም፡፡ እንደው ስለአንዳንዶቹ እንጂ በጠቅላይ ፍረጃ እንዳላረኩት ይሰመርልኝ እንጂ’ኮ ሰዎቹ ለውጥ ያላሳዩ “የባሰባቸው፤ ያው የትናንት ወጣቶች” ናቸው፡፡[13]

 

ፍርሀቴ ምንድን ነው? ይህ ትውልድን የማሳቀቅ አባዜ በ’ኛው ወንጌላዊው ሰፈርም አንድ… ሁለት… እያለ በግልጽ መታየቱ ብቻ ሳይሆን፣ ማቆሚያው ውሉም አልታይ ማለቱ ነው፡፡ እጅግ ያሳስባል፡፡ አስፈሪውን እውነት ዞር ዞር ብላችህ እዩ፤ በጊዜ ካልተመካከርን በቀር የሽማግሌ ሞገስ ያለቸው ሰዎች ቁጥር ከመኻላችንም አንድ በአንድ እየሳሳ ነው፡፡ እውነታውን ስንጋፈጥʼኮ በወንጌላውያን አማኞች ዘንድ የዛሬዎቹ ስሕተት ትምህርት አራጋቢዎችና ሐሰተኞችን ቀቢዎች እነኚሁ ዕድሜ ደጉ “ለፊታቸው ሽብሽባት፣ ለፀጉራቸው ሽበት” ያልነፈጋቸው አረጋውያን ናቸው፡፡[14] ምነው የዕድሜ ብዛት ለአንዳንዶች ማስተዋልን ያልሰጣቸው? በ“ለጌታ ወጣት መሆን፤ የተገፉ ወጣቶችን መደገፍ” ስም ስንቱስ ከነፈ? ለጌታ “ወጣት መሆን” ደግ፣ ነገር ግን ማስተዋልስ? ከነፋስ የሚቀድም ሩጫቸው ይልቅ መረጋጋትና አዙሮ ማየትስ? ጥበብ፣ ዕውቀትስ? የመጽሐፍ ቅዱሱ ወንጌል እውነትስ? የኢየሱስ ጌትነት መፈራትስ? “እንሰማዋለን” ያሉት መንፈስ ቅዱስስ? አንዳንዴም፡- “መካሪ የዕድሜ እኩዮች የላቸውምን? ለዚህ ባይደላን ባያድለን ነው?” እላለሁ፡፡ በዚህም በሌላም “ሊመካከሩ ፍቅሩም ጥረቱም ባይኖር” ይሆን የዕዳው ጫና ለሌላው የተረፈው? እውነቱን ደግመን ስንጋፈጥ ታዲያ ከዕድሜ ባለጸጋነት ሽልማታቸው በቀር ለመልካም ምስክርነት ያልበቁ ሰዎችን እንዲያው ዝም ብሎ በግርምትና በመሰቀቅ ማየት የብዙዎች ምርጫ ሆነ፤ ግን ለምን እንዲህ ይሁብን?

 

ለምንስ ሃያላን እንዲህ በዕድሜ ማምሻ ላይ ይወዳድቁ? በርግጥም ይህ እየታየ ያለው ችግራችን ከ”ረጅም ዕድሜ ጋር ተያይዞ ከሚመጣ ችግር” ጋር ይገናኝ ይሆን? ለዚህ መልስ በኖረኝ! “ለዚህ ዐይነቱስ አጓጉል ጉዳይ ከቃሉ መፍትሔው ምን ይሆን?”፤ “የሕክምና ሳይንሱስ ስለ አእምሮ መጋሸብ ችግር ምን ይላል? የአንዳንዶቹ ዝብረቃ ከዚህ ጋር ይያያዛልን?” ብለን ለመወያየትም ቅን የሆነ ፍላጎት ማሳየት አለብን፡፡[15] ይህ እና መሰሉ ጥያቄም የማንንም (የዕድሜ ባለጸጎችንም ጭምር) ስሜት ለመጉዳት የምንጠይቅ ሳይሆን “የአባቶች ወንጌላዊውን እምነትን ለሚቀጥለው ትውልድ በክብር ከማስተላለፍ ጥያቄ ጋር” የሚያያዝ በመሆኑ ነው፡፡ ይህ ነገን የማየት፣ የመሆን ወይም ያለመሆን ጥያቄ ነው፡፡ ተመልከቱ፡- የሌላ ሌላ ሥራ (የመንግሥትም) ቦታ ፍሬያማ “ዕድሜ”ን በገደብ ያስቀምጣል (ሰዎቹን ኋላ ላይ በክብር ይሸኛል)፤ ጥንቱን “ሰማዕትነት” ብዙዎችን በጊዜ ከዚህ ዓለም በክብር ያሰናብት ነበር (ያ ዛሬ ከሌለብን)፣ ከዚህ እየበዛ ከመጣብን ዘገምተኛ ዐደጋ ለመዳን ቶሎ ስለዚህ መራራ፣ ግን ደግሞ እውነተኛ ጥያቄ ላይ የግራ የቀኙን መነጋገር ተገቢ ይሆናል ባይ ነኝ፡፡

 

መልካሙን መንገድ ከማያሳዩ የዕድሜ ባለጸጎች መንጠንቀቅ

ራሳቸው የሐሰት ትንቢቶችን ስለ አገርና ስለ ግል ሕይወት ሳይሰቅቃቸው መናገርና መጻፍ ብቻ ሳይሆን፣ ነቢያት ተብዬ ተራ አጭበርባሪዎችን እንዲሁም የክፉ መንፈስ ቅባት ውጤት “ነቢያትን” እና ሳይላኩ “ሐዋርያት ነን” ባዮችን ዛሬ ዛሬ በየአደባባዩ የሚቀቡና የሚሾሙ (የአንድ ወቅቱ፣ የጥንቱ ወንጌል ዐርበኛ) ቄስ በሊና ሣርካን እና የሙሉ ወንጌል ቤተ ክርስቲያን የረዥም ዘመን ተወዳጅ አገልጋይ የነበሩት ፓ/ር በቀለ ወ/ኪዳንን ጨምሮ እነዚያን የዲያስፖራዎቹን ሁለት የክት ጎብኚዎቻችን[16] ጉዳይ ምን ማድረግ እንዳለብን ሙሉ በሙሉ መግባባት ላይኖረን ይችላል፡፡ ሁላችንም ስለ እነሱ እኩል አንገቶቻችንን አልደፋን ይሆናል፡፡ ልምድ ሆኖብን በመረጣ አንዱን አንግሥን፣ ሌላውን “በጠበልህ” ብለንም ይሆናል፡፡ ግን አንዳንድ ወጣት የቤተ ክርስቲያን መሪዎችን ከጤናማ አስተምህሮና መንፈስ ወጥተው ስናይ “ይህ ስሕተት ነው!” ማለት እንደቻልን ሁሉ፣ ዕድሜ ጠገቦችም በዚያው ስሕተት ቢገኙ መስፈሪያውና መለኪያው ግን አንድ መሆን አለበት ባይ ነኝ፡፡ በርግጥ!!

 

“ወደ እውነት መልሳቸው” እያልን በብርቱ የምንጸልየውና የምንማልደውም ስለእነዚህ አዋቂዎችም ጭምር ነዉ፡፡

 

በ“አባት አክብሩ ስም”፣ በፍቅር ስም፣ በመከባበር ስም፣ በኅብረት ስም፣ ወዘተርፈ… አቋም የለሽነትን ለሚያበረታቱ አንዳንዶች፣ ጎምቱ ሐሰተኞችን ከነስሕተታቸው መሸከምን እንደ “የአባት ዕዳ” ቆጣሪ ሌሎች እና እነዚያ ስሑታን ተማምለው እውነትን ከመሠረቱ ሲንዱ ላላመማቸው ግድ-የለሾች… የውስጥ ዐይን ብርሃን መለመን እንዳለ ሆኖ፣ ቅን ወንድሞችንና እኅቶችን ስለ ጕዳዩ ማሳሰብም የግድ ይሆናል፡፡ ፍቅርም እውነትን ወዳጅና ተዛማጅም ነውና ማስጠንቀቁም ተገቢ ነው፡፡ ከጸሎታችን ባሻገር ዋናው ነገር፡- ስሑታን “አባቶች” የየራሳቸውን የዕድሜ ዘመን በመልካም ላይጨርሱ ቁልቁል የተንደረደሩና የሌላውንም ሊያመክኑ ባለ-የለሌ ጉልበታቸው የሚታትሩ መሆናቸውን መገንዘብ፤ የቀራቸውንም ክቡር ዕድሜ ከንስሓ ሊያርቁ እልህ የተጋቡ መሆናቸውን መረዳታችን ነው፡፡ ስለሆነም ከሁሉም ዐይነት የዘመናችን ስሑታን - ከሳቱ “አባቶች”ም ጨምሮ እያልኩ ነው - ቤታችንን እንጠብቅ፤ ጊዜው ደግሞ እኛንና የእኛ የሆኑትን በብርቱ እንጠብቅ ዘንድም ግድ ይለናል፡፡

 

ከመልካሙ የእምነት መንገድ በአባትነት ስም ብዙዎችን እያወጡና እያሳቱ ባሉ ላይ እንነቃና ክፉ ስራቸውን እንሸሽ ዘንድ ዛሬ አልዘገየም፡፡

 

የቀረነው ግን ሩጫችንን በእውነት ቃል እና መንፈስ፣ በትዕግስትና በማስተዋል፣ በብርቱ ጸሎት በመልካም ሽምግልናና የዕድሜ ጸጋ መጨረስ ይሆን ዘንድ ቀሪዋን ጥቂት ዘመናችንን በወንጌል ምተራ መለካት ይሁንልን፡፡

ብዙ ብዙ ጸጋ!!

 

[1] Cyprian ከካርታጎ (Carthage) ነው ብለናል፡፡ ይህ የክርስቲያን መናኸሪያ የነበረው የሰሜን አፍሪካ ክፍል ዛሬ ቱኒዚያ በመባል በሚታወቀው አገር የተጠቀለለ ሲሆን፣ ሕዝቡ ከ98% በላይ ሙስሊም ነው፡፡

[2] የዳሲዮስ ዘመንን ስደት ለየት የሚያደርገው ሁሉንም የሮም ኤምፓየር ከሞላ ጎደል ማካለሉ ነበር፡፡ ሁሉም ዜጋ ለኤምፓየሩ ያለውን ታማኝነት ለማሳየት ለሮም አማልክት መስገድ ነበረበት፡፡ ለዚህም ማረጋገጫ ሠርተፊኬት (“libelli” ይሉታል) በእጁ መያዝ፣ ሲጠየቅም ማሳየት ነበረበት፡፡

[3] ጕዳዩ ቀላል አልነበረም፤ ሁለቱም ወገኖች የራሳቸውን አመራር መሥርተው ነበር፡፡

[4] ‘ያስረከብነው መጽሐፍ ቅዱስን አይደለም ፤ ተራ የመናፍቃን የመጻህፍትን ነው’ንጂ’ የሚል መከራከሪያ ግን ነባራቸው::

[5] በተያየ ምክንያት መቆየቱ ደግ ሆኗል፡፡        

[6] “ፓርላማ እንገባለን፤ ለኢትዮጵያ ህግ የምናወጣው እኛ ነቢያቱ ነን” ይላል አንዱ ለያዥ-ገናዥ ያሰቸገረ ሰው፡፡

[7] መጋቢ በቀለ ወ/ኪዳን ሪቫይቫል፡፡

[8] ሳያውቁና ለፓስተር አንፍሬ ባላቸው ፍቅር (እውነትም መስሏቸው) ወደ ትምህርት ቤቱ ገብተው የነበሩ ቅን ወንድም/እህቶችን ጌታ ረድቶ ተመልሰዋል፤ ሌሎችንም እርሱ ይርዳልን!!

[9] https://www.youtube.com/watch?v=-HNih3AlKVo&feature=youtu.be (ከ 25 ደቂቃ በኋላ ይመልከቱ)፡፡

[10]https://www.youtube.com/watch?v=npLRK75G2Ms ይህ መረጃ ከእምነት እንቅስቃሴ መምህራን ጋር ያላቸውን ህብረት ያሳያል፡፡ ፓስተር ዓለሙ ዘለቀ በትምህርት አቁዋማቸው የእምነት እንቅስቃሴን ከሚያራምዱ የጆን ሃጌ እና ኦራል ሮበርትስ ደጋፊዎች ውስጥ የሚመደቡ ናቸው፤ እስከማውቀው፡፡ ምናልባት ይህ ትምህርት ከጤነኛው መጽሐፍ ቅዱሳዊ ትምህርት ጋር ያለውን ሰፊ ልዩነት መገንዘብ የማይችሉም ሰው ይሆኑ ይሆናል፡፡ ቢሆንም ግን ሲጀምር ጥንቱኑ ይህን መሰል ችግር ካለባቸው… በዘመናቸው ማጠቃለያ ጊዜ ወንጌላዊያንን ማሸማቀቅ አልነበረባቸውም፤ ለመመለስ ግን ቀኑ ይኸው፡፡

[11] ክርስቶስ ሰምራ እግዚአብሔርንና ሰይጣንን ለማስታረቅ ብርቱ ጥረት ያደረገች ኢትዮጵያዊት ቅድስት ሴት እንደ ሆነች ገድሏን የጻፉት ያስተነትናሉ፡፡ “በክርስቶስ ሰምራ syndrome” ላይ አንድ ጽሑፍ መጻፍ ጀምሬአለሁ፡፡ በዚህ ጎራ በርግጥ ከአረጋዊያኑ ጎን ወጣቶችም አሉበት፡፡

[12] ተላላ አስታራቂ ሽማግሌ… ሰይጣንና አንድን መንፈሳዊ ሰው ለማስታረቅ ተመኘና … ለሰይጣን የሚለውን ብሎ መከረዉ፡፡ ለሰውዩውም፡- “ሰይጣን በስመ-አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ ሲባል ይሸሻል… እንግዲህ ከአሁን በኋላ ‹ስለ ፍቅር… በስመ-አብ ይቅር›፤ በሰላምና በየፍቅርም ኑሩ” አለ የተባለው ዐይነት ተረት መሆኑ ነው፡፡

[13] ዐለሙንና አካሄዱን አሁንም ተመልከቱ፤ ዛሬ ዛሬ አጓጉል እና ነውረኛ ስፍራዎች (በቲቪ የንግድ ማስታወቂያዎች) ላይም እንኳ ዕድሜ ጠገብ አዛውንት እያፈርን ማየት የተለመደ ሆኗል፡፡

[14] ቄስ በሊና ሣርካን እና ፓስተር በቀለ ወ/ኪዳን ተመልከቱ፡፡

[15] ይህ ጉዳዩ ብርቱና አሣሣቢ.. ነገ ከነገ ወዲያ ከቁጥጥር ውጪ መሆኑ የማይቀር በመሆኑ እንጂ አባትን ካለማክበር የሚመነጭ አይደለም፡፡ ለመነሻ ሃሳብም፡- ከ70 ዓመት በላይ የሆናቸው አገልጋዮች ከአደባባይ ከአገልግሎት ፈጽሞ ለመገለል ራሳቸው ቀድሞውኑ ቢያስቡበት (ካልሆነም ወንድም/እህት ወዳጅ ዘመድ ቢያሳስቧቸው) እላለሁ፤ ለመወያዬት መመካከር፡፡

[16] ፓስተር አንፍሬና ቄስ ቶሎሳ፡፡ ፓስተር ዓለሙ ዘለቀም ጉብኝቱን ጀምረዋል፤ ደጋግመው የሚመጡ(ብን) ከሆነ ሶስት ሊሆኑ ነው፡፡

Read 8530 times Last modified on Monday, 14 May 2018 15:03
Dr Afework

Email This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it.

Nahu's Corner

 

 

 

.

Right Now

We have 118 guests and no members online

About Us

Semayawi Thought is an online magazine published in Amharic and English, focused on contents to spiritual and personal growth.