የዝማሬ ሙዚቃ ወይም በአጠቃላይ የዜማ እና የቅኔው ዘርፍ በወንጌል አማኞች ዘንድ ያለው ስፍራ እጅግ በጣም ከፍተኛ ነው ማለት ይቻላል ለዚህም ማሳያው የትኛውም ቤተ እምነት አነስተኛ ሆነ ትላልቅ የአምልኮ ስብሰባዎችን ያለ ዝማሬ ለማከናወን አለመቻሉ እንዲሁም ለዝማሬ እየተሰጠ ያለው ሰአትና ትኩረት፤ እየተከፈለ ያለው ገንዘብና ሙያተኛ፤ በተለይ ለሙዚቃ መሳሪያዎች እና ለድምጽ ማጉያዎች እየወጣ ያለው ከፍተኛ ኢንቨስትመንት ለአብነት ይጠቀሳሉ።
ወንጌልን በማስፋፋት ሂደት ውስጥም ቢሆን ባለፉት ዘመናት ዝማሬ የነበረው ሚና አስደናቂ ነበረ። ከዚህም ባለፈ ዝማሬ አማኞችን በማጽናናት በማበርታት ከክፉ ጎዳና በመመለስ ለአምልኮ በማነሳሳት በማስተማር በተለይም ልጆችን ሊለካ የማይችል ሰፊ ፋይዳ የነበረው እና ያለው ድንቅ መንፈሳዊ የአገልግሎት ዘርፍ ነው።
በሙዚቃ ያልተጽናና ያልበረታ ያልታነጸ ማን አለ? ማንም ያልገባበትን ገጠር ገደላ ገደል በካሴት በሲዲ እየገባ ለስንቱ ነፍስ መዳን ምክንያት የሆነ ሚሲዮናዊ አይደለም ወይ ዝማሬ? ስንቱ ከሚታነቅበት ገመድ ወርዶ ስንቱ መርዙን ጥሎ ስንቱ ተስፋው ታድሶ በጌታ ጸንቶ ከክፉ ተመልሶ የለም ወይ በዝማሬ?
ይህ በእንዲህ እንዳለ ባለንበት ዘመን መንፈሳዊ ፋይዳው እና የአምልኮ መሳሪያነቱ ሳይሆን አዝናኝነቱ እንዲጎላ እየተደረገ ብዙ ቤተ እምነቶች ውስጥ አገልግሎቱ ያደገ እየመሰለ ነገር ግን እየሞተ ይመስላል። በተለመዱ መሳሪያዎች በተለመዱ ታዋቂ አዝማቾች በተሸመደዱ ሽብሸባ በሚመስሉ ጭፈራዎች ጩኸት እና የመደሰሰት አይነት ልምምድ ይህ ለወንጌል ትልቅ ሚና የነበረው ዘርፍ ዛሬ የኢንተርቴይመንት ኢንዱስትሪ እየሆነ የመጣ ይመስላል ይህ ጉዳይ አሳሳቢነቱ በከተሞች ላይ የጎላ ቢሆንም ገጠሩም በብዙ ችግር ውስጥ እየገባ እንደሆነ ልብ ልንል ይገባል።
በሌላ በኩል የድምጽ ማጉያ አጠቃቀማችን ከሳይንሳዊ መንገድ የራቀ በመሆኑ ጆሯችን መስማት ከሚገባው decibel (dB) የድምጽ መጠን መለኪያ ማለት ነው፤ ልክ ክብደት በኪሎ፤ ርቀት በሜትር እንደሚለካው ድምጽ ደግሞ ዴሲቤል ይለካል፤ ስለዚህ ጆሮአችን ከሚገባው ዴሲቤል በላይ እንዲሰማ እና ለጉዳት እንዲዳረግ ሆኗል። አሁን ባለው አካሄድ 80, 90, 100dB የሚደርስ ጩኸት ማለትም ለጠመንጃ ተኩስ ድምጽ ጥቂት የቀረው ጩኸት እየሰማን ብዙ እየተጎዳን ነው። ኮንፍራንሶች በግብታዊ ዝላይ፤ አቧራ ከማንሳት ያለፈ ነገር እስከማይኖር ድረስ፤ ወደ ቤት ይዘን የምንሄደው ነገር እየጠፋ ነው። ሰወችም ከአጥቢያ ህብረት እየራቁ ይገኛሉ። ለሙዚቃ ተብሎ የሚገጠመው መሳሪያ በብዙ ገንዘብ በብዙ ልፋት ቢሆንም ውጤቱ ሲታይ እንደቀድሞ ዘመን ሰው ተጽናንቶ ታንጾ ሳይሆን ተዝናንቶ ጨፍሮ ነው ቤቱ የሚገባው። በአንዳንድ ቦታዎች ደግሞ ነቢያት ለሚባሉት አይዶ ክቮቴሽን እንደ ማደመቂያ እነርሱ ሲያረፍዱ መጠባበቂያ ሲተነብዩ ማድመቂያ እንጂ የመዝሙር አገልግሎት እራሱን የቻለ አገልግሎት አይመስልም።